ቀሲስ ታምራት ውቤ: ዘሰአሊተ ምህረት
Print this page

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል ሁለት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

          ባለፈዉ ትምህርታችን የጌታችን የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አልፋና ዖሜጋ ፊተኛዉና ኃለኛው ከዘላለም እስከ ዘላለም ህያው የሆነ አምላክ መሆኑን በተረዳ ነገር አይተናል' በይቀጥላል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን ቻይ አምላክ መሆኑን በመጽሐፍ ቅዱስ ያለውን እውነታ ረድኤተ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ እናያለን፡፡

ሁሉን ቻይ :- ማለት እንዳሰበ የሚሠራ እንደፈቀደም የሚያከናዉን& ለሥራው ረዳት አጋዥ    አማካሪ የማይሻ& ሁሉን ከባህርይ የሚያከናውን& በሰማይም ሆነ በምድር ከምድርም በታች በሁሉ የሚሠራ& በሁሉ የሚያዝ በሁሉ ላይ የሠለጠነ &ማንም ማን ለምን ይህን ታደርጋለህ ብሎ ሊከለክለዉ ሊያግደው ሊያስቆመው የማይቻል& በአጠቃላይ ይበልጥ ገላጭ በሆነ ቃል "የሚሳነው ነገር የሌለ" ማለት ነው፡፡ ጥያቄዉ ሁሉን ቻይ የሚለው የአምላካዊ ባህርይ መገላጫ ቅፅል ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ይገባዋል ወይ? የሚል ነው፡፡ የኦርቶደክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያንም መልስ እንዴታ ይገባል ነው!!!

ማስረጃ

ትን.ኢሳ 9*6 ህፃን ተወልዶልናልና……ስሙም ድንቅ መካር ኃያል አምላክ የዘላለም አባት                  የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡ ኃያል አምላክ የሚለው ቃል የተወለደው በሥጋ የተገለጠው እርሱ ሁሉን ቻይ አምላክ መሆኑን የሚያስረግጥ ነው፡፡

ዮሐ 1*3 ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም፡፡

          በዚህ ቃልም በቅደምና የነበረው ቃል በኋለኛው ዘመን ሥጋን የተዋሃደው ቃል ሁሉን የፈጠረ ሁሉን ያስገኘ ምንም ምን ያለእርሱ የሆነ እንደሌለ የሚያስረዳ ነው፡፡

ቆላ 1*15 እርሱም የማይታይ አምላክ ምሳሌ ነው የሚታዩትንና የማይታዩትም ዙፋናት ቢሆኑ ወይም ጌትነት ወይም አለቅነት ወይም ሥልጣናት በሰማይና በምድር ያሉት ሁሉ በእርሱ ተፈጥረዋልና ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኩር ነው፡፡ሁሉ በእርሱና ለእርሱ ተፈጥሯል እርሱም ከሁሉ በፊት ነው፡፡

የማይታ አምላክ ምላሌ ሲል አምላክ አይደለም ማለቱ አይደለም፡፡ "በሰው ምሳሌ ሆኖ" ሲል ሰው አልሆነም ለማለት እንዳለሆነ ሁሉ ፊል 2*6-8 ሁሉ በእርሱ እንደተገኘ ለእርሱ ክብርም እንደተፈጠረ በመግለጥ ሁሉን ቻይነቱን መሠከረ፡፡

      ፅንስቱ ሁሉን ቻይነቱን ሲያስረዳ

       ምድር ያለ ዘር ሴት ያለወንድ ትፀንስ ዘንድ ሕገ-ተፈጥሮ አይፍቅድም፡፡ ሁሉ የተገኝ በዚሁ የተፈጥሮ ሥርዓት አልፎ ነው፡፡ የጌታ ፅንት ግን እንዲህ አይደለም ወንጌላዊው ማቴዎስ" ለዮሴፍ ታጭታ ሳለች ሳይገናኙ በመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ ተገኘች" እንዳለ የጌታ ፅንስ ከሦስት ግብራት ንፁህ ነው፡፡ ይኸውም ዘር&ሩካቤ&ሰስሎተ ድንግልና ነው፡፡ጌታችን ሲፀነስ ሩካቤ አልተፈፀም፡ዘርዐ ብእሲ አላስፈለገም የእመቤታችን ድንግልናም አልተለወጠም፡፡ በዚህ እውነትም የተወለደልን ህፃን ኃያል አምላክ ወይም ሁሉን ቻይ መሆኑን ገለጠልን፡፡       ማቴ 1*18-25 & ሉቃ 1*26-56

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደቱ ሁሉን ቻይነቱን ሲያስረዳ

      የጌታ ልደቱ እንደ ፅንሠቱ ሁሉ ልዩ ነው በልደቱ የእናቱን ድንግልና አልለወጠውም ምጥ ጭንቅ አላገኛትም፡፡ ሰው በር ከፍቶ ወጥቶ ከኋላዉ እንዲዘጋዉ የእርሱ ልደት እንዲህ አይደለም ማኅተመ ድንግልናዋ ለቅፅበተ ዓይን እንኳን አልተለወጠም ይህ እንዴት ይሆናል? ለሚል

-ጌታ በተዘጋ ቤት ጣርያ ሳይነቅል ግድግዳ ሳያፈርስ መሠረት ሳየቆፍር በር መስኮት ሳይከፍት እንዴት ከሐዋርያት መካከል እንደተገኘ ይመርምር፡፡ ሉቃ 24

ትን.ሕዝ 44*1-3 ወደ ምሥራቅ ወደሚመለከተው በስተውጭ ወዳለው ወደ መቅደሱ በር አምጣኝ ተዘግቶም ነበር እግዚአብሔርም ይህ በር ተዘግቶ ይኖራል እንጂ አይከፈትም ሰውም አይገባበትም የእስራኤል አምላክ ገብቶበታልና ተዘግቶ ይኖራል፡፡

             ምሥራቅ እመቤታችን የእውነተኛዉ ፀሐይ መውጫ ናትና& መቅደሰ የማኅፀንዋ 9ወር ከ5ቀን ተመስግኖበታልና& በር የማኅተመ ድንግልናዋ ተዘግቶ ይኖራል ማለቱ ለዘላለም እናትነትን ከድንግልና አስተባብራ ፀንታ መኖርሯን ሲገልጥ ነው፡፡

መዝ.ዳዊ 146*1-2 ኢየሩሳሌም ሆይ እግዚአብሔርን አመስግኚ ጽዮንም ሆይ ለአምላክሽ እልል በይ የደጆችሽን መወርመርያ አፅንቷልና፡፡ /በዚህ ጥቀስ ኢየሩሳሌም ጽዮን የተባለች እመቤታችን የታላቁ ንጉሥ ከተማ ናትና& የደጆችሽ መወርወርያ የተባለ ማኀተመ ድንግልናዋ ነው አፅንቶ እንደሚጠብቀው ግልጽ ሆኗል፡፡

ኢሳ 66*7 ሳታምጥ ወለደች* ምጥም ሳያገኛት ወንድ ልጀን ወለደች ከቶ እንዲህ ያለ ነገር ማን ሰምቶአል? እንዲህ ያለ ነገርስ ማን አይቶአል?

የህፃንነት እድሜው

           በተዐምረ ኢየሱስና በተለያዩ የቤ/ክ መፃህፍት እንደተገለጠው ጌታ በህፃንነቱ ይፈፅማቸው የነበሩ ተዐምራቶች ሁሉን ቻይ አምላክ ለመሆኑ ማስረጃዎች ናቸው፡፡ በመፅሐፍ ቅዱስም ከሩቅ ምሥራቅ የመጡትን የጥበብ ሰዋች በኮከብ መምራቱ ሊቃውንትን በሚጠይቀው ጥያቄና በሚሠጠው መልስ ማስደመሙ በተፈጥሮ ላይ ያለውን ሥልጣን እውቀቱም የባህርይ መሆኑን ያስረዳል፡፡

ይቆየን!

                                    ወስብሐት ለእግዚአብሔር

                                    ቀሲስ ታምራት ውቤ

 

                                    ጥቅምት 2005ዓ.ም

© - 2026