በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ብርታትና ድካም፣ ማግኘትና ማጣት፣ስኬትና ውደቀት፣ ሰላምና ሁከት፣ ጤናና ህመም ሲፈራረቁብን ከረምን፡፡ የመጡትን በመቀበል ደስታና እንደየ ሥራቸው የተጠበቀላቸውን ለመቀበል በሞት ወደ ጌታ የሄዱትን በመሸኘት በሀዘን ስሜታችን ሲቆስልና ሲፈወስ ሲያር እና ሲታደስ ባጅተን አዲሱ ዓመት ዋዜማ ላይ ላደረሰን አምላካችን ሸክላ ሕይወታችን ጥላ መሆኑን ዘንግተን ዛሬም እንደ አምና አዲሱን ዓመት በአሮጌ መንፈስ ለመቀበል ለተቃረብን ሁሉ የጌታ መንፈስ ቅዱስ መልዕክት እነሆ፡፡
‹‹በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት›› ሉቃ 13፡6-9
በአንድ ወቅት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶሰ በማስተማር ላይ ሳለ ጲላጦስ በመሠዊያው ላይ በሰይፉ አርዶ ደማቸውን ከመሥዋዕታቸው ጋር ስለደባለቀው ሰዎች ዘግናኝ ፍጻሜ ሊነግሩት ጀመሩ፡፡ ጌታችንም መልሶ እነዚህ ሰዎችና በሰሊሆም ግንቡ ተንዶባቸው የሞቱ ሰዎች ሁሉ ከእናንተ ይልቅ ኃጢአት የሠሩ ይመስላችኋል፤ ንስሓ ባትገቡ ሁላችሁ እንደዚሁ ትጠፋላችሁ በማለት አስጠንቅቋል፡፡
ተፈጥሮአዊ በሆነ ሁኔታም ሆነ አሰቃቂ በሆኑ ሰው ሠራሽ አደጋዎች ብዙ ሰዎችን ከኋላችን ትተን ጽድቅና ኃጢአት ከሚፈራረቁበት መሬት ሥር ቀብረን እኛ ቆመናል ዛሬ ላይ ደርሰናል፡፡ ነገርግን አዚህ የመደረሳችን ምስጢር እኛ ከእነርሱ ተሽለን መገኘታችን ይሆን?
ጌታችን ለጥቆ በወይኑ እርሻ ተተክላ ሦስት ዓመት ሙሉ ፍሬ ስላልተገኘባትና እንድትቆረጥ ከተሰጠባት ትዕዛዝ በወይኑ አትክልተኛ ጸኑ ልመና ሰለዳነች በለስ ማለፊያ የሆነ ምሳሌ በመስጠት የእኛን እዚህ የመድረስ ምስጢር ገልጾልናል፡፡
የወይኑ ባለቤት በለሷ ሦስት ዓመት ባለማፍራቷ እንድትቆረጥ ትዕዛዝ የሠጠው በርሷ አለማፍራት ብቻ ሳይሆን ምድሩንም እያጎሳቀለች በመሆኗ ጭምር ነበር፡፡ የወይኑ አትክልተኛ ግን በጌታው ፊት ቀርቦ ዙሪያውን እስክኮተኩትላትና ፍግ እስካፈስላት በዚህ ዓመት ደግሞ ተዋት ወደፊት ብታፈራ ፣መልካም ነው ያለዚያ ግን ትቆርጣታለህ በማለት ከመቆረጥ አድኗታል፡፡
መተርጉማን አንድ ሰው የተባለ ጌታ እግዚአብሔር፣በለስ የተበሉ ቤተ እስራኤል፣ የወይን እርሻ የተባለች ቤተመቅደስ የታነጸባት ኢየሩሳሌም፤ ሦስት ዓመት የተባለ ዘመነ መሳፍንት፣ዘመነ ነገሥት ዘመነ ካህናት መሆኑን ያትታሉ፡፡ ጌታ እግዚአብሔር ተስፋ በተሰጣቸው ሕግ በተሠራላቸው በእስራኤል ዘንድ ሃይማኖት ምግባር አገኝ እንደሁ ብሎ በብሉይ መምህራን አድሮ ቢመጣ አጣባቸው፡፡
መጋቤ ብሉይ ቅዱስ ሚካኤልን ለሌላው ክፉ አብነት ሆነው እንዳያስጎዱ አጥፋቸው ብሎ ቢናገርም ቅዱስ ሚካኤል ተራድቼ ምግባር እስካሠራቸው ታገሥ ብሎ በለመነው ልመና ለመትረፋቸው ምሳሌ ነው፡፡ በፋርስ፣በባቢሎን፣የገጠማቸው ስደት ጨርሶ አላጠፋቸውምና፡፡
አንደም አንድ ሰው የተባለ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ፡ በለስ የተባሉ አይሁድ፣ ሦስት ዓመት የተባሉ ጌታ በሥጋ ተገልጦ ያስተማረው ሦስት ዓመት ነውና ነው፡፡ በዚህ ጊዜ የቃሉን ትምህርት የእጁን ተአምራት ዓይተውከክፋታቸው መመለስ መልካም ፍሬ ማፍራት ስላልቻሉ የወይኑ አትክልተኛ የተባለው መጋቤ አዲስ ቅዱስ ገብርኤልን አጥፋቸው ቢለው ምንም እንኳ በጥጦስ ቢማረኩም ፈጽሞ ከመጥፋት አማልዶ እንዳዳናቸው የሚያሳይ ነው፡፡
አንድም አንድ ሰው የተባለው ጌታ በለስ የተባልን በስሙ አምነን የተጠመቅን ክርስቲያኖች ነን፡፡ ሦስት ዓመት የተባለ የሰው የእድሜው ዘመናት ናቸው፡፡ ይኸውም ሕጻንነት፣ውርዝውናና ዕርግና ናቸው፡:፡ ጌታ በእነዚህ የእደሜ ዘመናችን ሁሉ መልካም ፍሬ አፍርተን እንገኝ ዘንድ ይጠብቅብናል፡፡ እንድም በሦስቱ ክፍላተ ጊዜያት በነግህ፣በሰርክ፣በሌሊት መልካም ሥራ ይጠበቅብናል፡፡ ባለን ጊዜ ጠባቂ መልአካችንን ነፍሳችንን ከሥጋችን እንዲለይ ‹‹ቁረጣት›› ብሎ ማዘዙን ያሳያል ጠባቂ መልአኩ ግን ጌታ እግዚአብሔር ዕድሜ ለንስሓ እንዲሰጠን ‹‹ በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት›› በማለት ይለምናል፡፡
ጠባቂ መልአኩ ‹‹ በዚች ዓመት ደግሞ›› ማለቱ ተመሳሳይ ልመና ብዙ ጊዜ ማቅረቡን ያመላከታል፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ልመና ቅዱሳንንና መላእክት ምን ያህል ጊዜ አቅርበውልን ሕይወታችንን ታደገዋት ይሆን?
በተጨማሪም የወይን ጠባቂው ካህናትን ይወክላል፡፡ የእምነት ፍሬ ያልታየባቸውን የስም ክርስቲያኖች ለሌሎቹ መጥፎ አርአያ እንዳይሆኑ ከምእመናን አንድነት ለይዋቸው በተባሉ ጊዜ እንደ መኮተኮት ፍግ እንደማፍስስ መክረን አስተምረን መልካም ሥራ እንድናሠራቸው ታገሰን በማለት በሚያቀርቡት ጸሎት በሚሠውት መሥዋዕት መማጸናቸውን ያመለክታል፡፡
ይቺን በለሰ ማወቅ ራስን ማወቅ ነውና ቀርቤ እመረምራት ዘንድ ወደደኩ፡፡
፩. የመጀመርያው በለሲቱ ፍሬ ለማፍራት የሚያስችላት ማንኛውም ነገር ተሟልቶላት ነበር፡፡ ሁኔታዋን በቅርበት የሚከታተል ጠባቂም ነበራት ነገር ግን ፍሬ አልተገኘባትም፡፡ እኛም መልካም ፍሬ እንድናፈራ የሚያስፈልጉን ሁሉ ተሟልተዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ፣ቅዱሳት መጻሕፍት፣ምሳሌ የሚሆነን የቅዱሳን ሕይወት፣ካህናትና መምህራን፤ ከዚያም በላይ የቅዱሳን መላእክት እርዳታና በእኛ ውስጥ የሚሠራ የእግዚአብሔር ቅዱስ መንፈስ አለ፡፡ ግን በአንዱም ተጠቅመን መንፈሳዊ ፍሬ ልናፈራ አልቻልንም፡፡ ጌታ እግዚአብሔር ከእኛ ፍሬ የሚጠብቀው ከእርሱ የሚጠበቅበትን ከፈጸመ በኋላ ነው፡፡ ኢሳ 5፡1
፪. በለሷ ከሩቅ ሲያይዋት ልምላሜ ስለነበራት ፍሬ አይኖራትም ተብሎ አልተጠበቀም፡፡ ደረቅ ብትሆንማንም ፍሬ አይፈልግባትም ነበር፡፡ ይህ ቅጠል ወይም ልምላሜ በእኛ ሕይወት ያለ ‹‹መስሎ መታየት›› ነው፡፡ ቤተክርስቲያን በመመላለስ፣በማስቀደስ፣በሽንገላ ከንፈር፣ጉባኤ በመካፈል ወዘተ…ብቻ የተወሰነ ሕይወት ነው፡፡ ይህ የንሰሓ ፍሬን የሕይወት ለውጥን የመንፈስ መታደስን ካለመጣ በራሱ ዋጋ ሊያሰጥ አይችልም፡፡ ክርስቲያን የተባልነው ሆነን ለመገኘት ፍሬ ለማፍራት ነው፡፡ የመንፈስ(የክርስትና) ፍሬ የተባሉትም በገላትያ 5፤22 የተጠቀሱትና እነርሱን የሚመስሉ ምግባራት ናቸው፡፡
፫. የበለሷ ጌታ ከበለሷ ፍሬ ፈልጓል፡፡ አንድ ሰው ካህን ከሆነ የክህነት፣መነኩሴ ከሆነ የምንኩስና፣ሰባኪ ዘማሪ ከሆነ የአገልጋይነት፣ሰንበት ተማሪ ከሆነ የደናግላን በአጠቃላይ ክርስቲያን ከሆነ የክርስትና ፍሬ ይታይበት ዘንድ ግድ ነው፡፡ ስም ብቻ መሸከም ክብር አያሰጥም፡፡
ለምሳሌ፡- አንድ መንግሥት በሌላ ሲተካ የቀድሞው መንግሥት የጦር ጀነራሎች፣ኮሎኔሎች፣ሻለቆችወዘተ…ይኖራሉ፡፡ ሁሉ በአዲስ ሲተኩ ሥልጣናቸው ይውሰድና ስም ብቻ ተሸክመው ይቀራሉ፡፡ የሚያዙት አንድ ወታደር ሳይኖር ታሪክ ብቻ እያወሩ ሕይወታቸውን ይገፋሉ፡፡ ስሙ ሥራ ካልሠራ ለመጠሪያነት መለጠፉ ነበርኩ ከማለት ውጪ ለምን ይጠቀማል?እኛም ክርስቲያን ተብለን ታላቅ ስም የተሸከመን መጠሪያ ብቻ እንዲሆነን ወይም ያለፈ ታሪክ ለመተረክ ሳይሆን ትቆርጣታልህ ሲባል እስከመቼ?
እንኪያስ ፍሬ እንዲገኝብን ምን እናድርግ?
፩.ሁልጊዜ የጌታ እግዘአብሔርን ቃል በማስተዋል በማንበብ ሕይወታችንን ማሳደግ ‹‹ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ ደስይለዋል ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያስባል እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደተተከለች ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል››መዝ ፩÷፪-፫
፪.ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ፍጹም ሕብረት ያለው ሕይወት ለመምራት መጣር ይህም የቃሉን ትምህርትና የሕይወቱን አብነት በማየትና እርሱን ለመምሰል ራስን በማስለመድ የሚገኝ ነው፡፡ ጌታችን ሲመክረን‹‹ እውነተኛ የወይን ግንድ አኔ ነኝ ገበሬውም አባቴ ነው ፍሬ የማያፈራውን በእኔ ያለውን ቅርንጫፍ ሁሉ ያሰወግደዋል ፍሬ የሚያፈራውንም ሁሉ አብዝቶ እንዲያፈራ ይጠራዋል… ‹‹ በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ፡፡ ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም፡፡ እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናነተም ቅርንጫፎች ናችሁ ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል፡፡ በእኔ የማይኖር ቢሆን እንደ ቅርንጫፍ ወደ ውጭ ይጣላል ይደርቅማል፡ እነርሱንም ሰብሰበው ወደ እሳት ይጥሏቸዋል ያቃጥሉአቸውማል፡፡›› ክርስቲያን ተብሎ የክርስቶስ ኢየሱስ ቃሉንና ሕይወቱን የማይከተል ቢኖር የተገነጠለ የደረቀ ወደ እሳትም ለመጣል የተዘጋጀ ቅርንጫፍ ነው፡፡ ዩሐ ፩፭÷፩-፭
፫.ጸሎት፡- በሥርዓተ ቅዳሴ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውና ክብር ደሙ ለዘላለም ሕይወት ሲታደል በዜማ በሚጸለየው ጸሎት ላይ ‹‹ ሀበኒ እግበር ፍሬ ዘያሠምረከ›› እንላለን፡፡ አንተን ደስ የሚያሰኝ ፍሬ ሃይማኖት እሠራ ዘንድ ኃይል መንፈሳዊ ስጠኝ በማለት በሥጋው እና በደሙ እንማጸናለን፡፡ ይህም የተወደደና የተጋባ ጸሎት ነው፡፡
ዮሐንስ መጥምቅ ለአይሁድ‹‹ እናንተ የእፉኝት ልጆች ከሚመጣውቁጣ እንድትሸሹ ማን አመላከታችሁ; አንግዲህ ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አድርጉ…›› በማለት ከገሠጸ በኋላ አብርሃም አባትአለን የሚሉት ከንቱ ትምክህት አብርሃማዊ ሃይማኖትና የመንፈሳዊ ፍሬ ካልተገኘባቸው ሥልጣነ እግዚአብሔር ከአብረሃም ልጅነት ቆርጦ እንደሚጥላቸው አስጠንቅቋቸዋል፡፡ በእኛ እንዲሁ ነው፡፡ በስሙ ክርስቲያን ተብለናል ከእመቤታችን በጸጋ ተወልደናል የቅዱሳን ቤተሰብሆነናል ካልን በእነርሱ የታየ ሕይወት ሊታይብን ግድ ነው፡፡ ካለበዚያ አንቆረጣለን፡፡
፬.የበለሷ ጌታ የበለሷ ፍሬ አለማፍራት ብቻ ሳይሆን ያሳሰበው ያለ ፍሬ በመቆየቷ ምድሩን ጭምር እያጎሳቆለች በመሆኑም ነው፡፡በመጀመሪያው የክርስትና ዘመናት አህዛብ ወደ ክርስትና በእጅጉ ይስባቸው የነበረ የክርስቲያኖች ስብከት ብቻ ሳይሆን ይታይባቸው የነበረው ተወዳጅ ምግባር ነበር፡፡ ክርስቲያኖች በፍቅራቸው፣በትዕግስታቸው፣በትኅትናቸው፣በታማኝነታቸው፣ሀሰትን፣ዝሙትን፣ርኩሰትን፣ፍርድ ማጉደልን፣መማለጃ(ጉቦ)መቀበልን፣ዘፈንና፣ስካርን ጠብንና ክርክርን፣ተንኮልና አድመኝነትን፣ትዕቢትንና በሌሎች ላይ መፍረድን ወዘተ… በመጥላታቸው ይታወቁ ነበር፡፡ በሰላም ሆነ በመከራ ጊዜ በማግኘትም ሆነ በማጣት፣በሞትም ሆነ በሕይወትም ፍቅራቸው የማይቀዘቅዝ ደስታቸው የማይበረዝ ነበር፡፡ ስለዚህ ብዙዎችን በሕይወት በሚገለጥ ስብከት እስከ ሞት ለታመኑት አምላክ ማርከዋል፡፡ ዛሬ ግን እኛ ክርስቲያኖች እንደሚጠበቅብን ባለመሆናችን እንኳን ከውጭ ያሉት ተማርከው ሊገቡ ከውስጥ ያሉት እየወጡ ተቸግረናል፡፡
ፍሬ አለማፍራታችን ከራሳችን አልፎ ለሌሎችም የማሰናከያ ድንጋይ ስለሚሆን ነው‹‹ቁረጣት›› የሚል ትዕዛዝ ከልዑሉ የሚወጣው፡፡ የቅዱሳን ምልጃ የመላእክትና የካህናት ጸሎት ጌታ እግዚአብሔርን ከመዓት ወደ ምህረት ከቁጣ ወደ ትዕግሥት ባይመልሰው በዚህች ደቂቃ ይህን ጹሑፍ ለማንበብ እንኳ አንበቃም ነበር፡፡
ከእኛ ቀድመው የተጠሩ ፍሬ ተገኝቶባቸው ወይም ምድሪቱን በክፋት ሥራ አጎሳቁለው እንደተጠሩ የሚያውቅ ጠሪው ብቻ ነው፡፡ እኛ ለመፍረድ እውቀቱም ሥልጣኑም የለንም፡፡
እኛ ግን የቆየነው ከሁለቱ ባንዱ ምክንያት ነው፡፡ መንፈሳዊ ፍሬ ተገኝብቶናል አልያም ‹‹ቁረጣት›› ተብሎ የመላእክቱና የቅዱሳን ምልጃ ታድጎናል፡፡ ግን ስለ እኛ በዚህ ዓመት ደግሞ ተዋት ወደፊት ብታፈራ ደህና ነው ያለዚያ ግን ትቆርጣታለህ፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹የአህዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋም ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል›› ሲል መስክሯል ባለፈው ዓመት ግብረ አህዛብን ለመፈጸም ለመዳራት፣ለስካር ለሥጋ ምኞት፣ለዘፈን፤ሀሰት ለመናገር ወዘተ… ጊዜ፣ገንዘብ፣ኃይል፣ ቁርጠኝነት፣ሕብረት ከነበረን ለሚያግደን ምክንያትም መንገድ እንዳልሰጠን ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም፣ራስን ለመግዛት፣በወይን ጠጅ ሳይሆን በመንፈስ ለመሞላት፤ለመንፈሳዊ ምኞት፣ለዝማሬ፣ እውነትን ለመመስከር፣ለሚሰድቡን ለመጸለይ በሌሎች ላለመፍረድ ወዘተ…ጊዜ፣ገንዘብ፣ኃይል፣ቁርጠኝነት፣ሕብረት፣ምክንያትን መሰበር በእኛ ዘንድ ሊገኝ የተገባ ነው፡፡ በዚህ ከመቆረጥ እንድናለን፤ለምንኖርባት ምድር መልካም አርአያ እንሆናለን ጊዜያችን ደርሶ ብንሄድም የሕይወትን ጽዋ እነቀበላለን ከቅዱሳን ሕብረትም እንደመራለን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ቀሲስ ታምራት ውቤ
2006ዓ.ም.