Login
Main menu

ታሪከ አበው: አዳም እና ሄይዋን ክፍል 1

Download
Name
Play
Size
Duration
download
AdamAndEve

107 MB
1:56:55 min

Read more...

በአዲስ ዓመት መልካም አዲስ ሕይወት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ይህንን መልዕክት ከማንበቦ በፊት ‹‹ በዚህች ዓመት ደግሞ ተዋት›› በሚል የተጻፈውን መልዕክት  ያነቡት ዘንድ በእግዚአብሔር ስም እንጠይቃለን፡፡

‹‹ነገ እንደ ዛሬው ወደ አንተ እመጣለሁና ተዘጋጅ››

 

 

Read more...

የተሻለ ምርጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

    በተለያየ አህጉር አንድ ጊዜ ስለተሠጠች የቅዱሳን ሃይማኖት እየተጋደላችሁ፤ ዲያብሎስንና ሥራውን ሁሉ በእምነት ኃይል እየተቃወማችሁ የጌታችንን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ዳግም መምጣት በተስፋ ለምትጠባበቁ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ አእምሮን ሁሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

   ባለፉት ጊዜያቶች በላክሁላችሁ ጦማሮች ቅዱስ እግዚአብሔርን በመከተልና፤በቅድስና ስፍራው በቤቱ በመገኘት የምናገኘውን መልካም ነገርና፤ ምርጫችንም ምን መሆን እንዳለበት ተነጋግረናል፡፡ ለዛሬ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በገለጠልን መጠን ሌላ ሦስተኛ ጠቃሚ ነጥብ አናያለን፡፡

ከብዙ ወርቅና ብር ይልቅ የአፍህ ሕግ(ቃል) ይሻለኛል መዝ118፥70

   ነብዩ ዳዊት በዚህ የመዝሙር ቃሉ ሁለት በሰው ዘንድ ከፍተኛ ትኩረት የሚስቡ (የሚወደዱ) እንዲሁም አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን አነፃጽሯል፡፡ አንዱ ጊዜያዊ ሌላው ዘላለማዊ፣ አንዱ ምድራዊ ሁለተኛው ሰማያዊ፣ ላንደኛው ከተገዛን ወደ ጥፋት የሚወስደን ሁለተኛው ግን ከጠበቅነው የሚጠብቀን ዘላለማዊ ክብርንም የምናገኝበት ነው፡፡ አስቀድመን የመጀመርያውን እንይ፡-

ብርና ወርቅ፡- በዓለማችን ስለ ብርና ወርቅ ተብሎ የሰው ልጅ የሆነውንና ያደረገውን ከመናገር ያልሆነውንና ያላደረገውን መናገር ይቀላል፡፡ የሚነገር ከተገኘ፡፡ ብዙ ሀገር ፈርሷል፤በርካታ ህዝብ ለባርነት ፈልሷል፤ለነፃነትና ለክብር ሳይሆን ለወርቅና ለብር ሲባል ብዙ ጦርነት ተካሂዷል ብዙ ንፁህ ደም ፈሷል፡፡ ከቤተመንግስት እስከ ቤተክህነት፣ ከንጉሰ እስከ ጳጳስ ፣ ከግል እስከ

 

ቡድን ተንኮል ገምዷል ሴራ ሸርቧል፡፡ ወላጆች ልጆቻቸውን ልጆች ወላጆቻቸውን፣ ባለትዳሮች የፍቅር የኑሮ አጋሮቻቸውን ከድተዋል ለሞትም ዳርገዋል፡፡ በዘመናችንም ብዙ ይደረጋል፡፡

 በአጠቃላይ የቀን ቅዥታችን የሌሊት ህልማችን ዕለት ተዕለት የምንባክነው ብርና ወርቅ ለማግኘት ነው፡፡ በዚህ ዘመን ለብርና ለወርቅ ክብሩን ያልጣለ ማግኘት ይቸግራል፡፡ሴቶችና ወንዶች ለገንዘብ ክቡር ሰውነታቸውን ለዝሙት ሽጠዋል፡፡ እንኳን ሌላው ራሳቸው የሆኑትንና የሚፈፀምባቸውን ለመግለፅ እስኪቀፋቸው ተዋርደዋል፡፡ ህፃናት በመጫወቻ ዕድሜያቸው በሴሰኝነት ራሳቸውን በሳቱ ባለፀጋዎችና በገንዘብ ላበዱ ጨካኞች መጫወቻ ሆነዋል፡፡ ገንዘብ እንዲሞላ ሀብት እንዲሠምር ሰዎች እንደከብት ታርደው መሥዋዕት ሆነዋል፤ደማቸውም ለዲያቢሎስ ግብር ቀርቧል፡፡ የሚብሰውም ሰው በምድር በሰማይ የሚከብርበትን ከፈጣሪው ጋር አንድ የሚሆንበትን ሃይማኖቱን ሳይቀር በብርና ወርቅ ለውጧል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም "ገንዘብ በመመኘት ይረቡባችኋል" ቅዱስ ጳውሎስም "…ዳሩ ግን ባለጠጎች ሊሆኑ የሚፈልጉ በጥፋትና በመፍረስ፤ ሰዎችን በሚያሰጥምና በሚያሰንፍ በሚጎዳም በብዙ ምኞትና በፈተና በወጥመድም ይወድቃሉ፡፡ ገንዘብን መውደድ የክፋት ሁሉ ሥር ነውና፤አንዳነዶችም ይህን ሲመኙ ከሃይማኖት ተሳስተው በብዙ ሥቃይ ራሳቸውን ወጉ፡፡" ብለዋል፡፡ስለ ብርና ወርቅ ይህቺ ዓለም ምንያህል ርኲሰትን ተሸከመች፤ ፈጣሪስ የቱን ያህል ታገሠን፡፡ 2ጴጥ 2፥3፤1ጢሞ 6፥6-10

   ጌታም አስቀድሞ "ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል ወይም ወደአንዱ ይጠጋል፤ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም" ሲል አስጠንቅቆናል፡፡ ማቴ 6፥24

 

   እንዲህም ሆኖ ብርና ወርቅ እርካታን ሰጥቶን፣ ከደዌ ፈውሶን፣ ሰላምን አስገኝቶልን እውነተኛ ወዳጆችን አቅርቦልን፣ ይልቁንም ከሞት አድኖን ከእግዚአብሔር ቁጣም አስጥሎን አያውቅም፡፡ ይልቁንም በተቃራኒው ነው፡፡ " ታላቁ የእግዚአብሔር ቀን ቀርቧል…ያ ቀን! የመዓት ቀን፣ የመከራና የጭንቀት ቀን ፣ የመፍረስና የመጥፋት ቀን ፣ የጨለማና የጭጋግ ቀን ፣ የደመናና የድቅድቅ ጨለማ ቀን ፣ በተመሽጉ ከተሞችና በረዘሙ ግንቦች ላይ የመለከትና የሰልፍ ጩኸት ቀን ነው፡፡ በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ሠርተዋልና ሰዎችን አስጨንቃለሁ፤እንደ ዕውርም ይሄዳሉ፤ ደማቸውም እንደ ትቢያ፤ ሥጋቸውም እንደ ጉድፍ ይፈስሳል፡፡ በእግዚአብሔር ቁጣ ቀን ብራቸውንና ወርቃቸው ሊያድናቸው አይችልም…" ትን.ሶፎ 1፥14-18

   እንግዲህ ብዙ የምንሆንለትና የምናደርግበት ብርና ወርቅ ኃይሉና ጉልበቱ እዚህ ድረስ ነው፡፡ አንባቢው ያስተውል በደዌ የሚማቅቁ በሰላም እጦት የሚሳቀቁ በሞትና በእግዚአብሔር ፍርድ ሳያስቡት ድንገት የታነቁ ብዙ ባለፀጋዎች ከእኛ በፊት አልፈዋል፡፡ በጊዜው ካልነቃን በእኛም የሚደርስ ይኸው ነው፡፡ የሰው ሕይወቱ በገንዘቡ ብዛት አይደለምና፡፡ ሰው ዓለሙን ቢያተርፍ ነፍሱን ካጣ ምን ይጠቅመዋል፤ ስለ ነፍሱስ ምን ቤዛ ይሠጣል? ሉቃ 12፥13-21፣ማቴ 16፥26-27

በአንፃሩም በተሠጠን ገንዘብ መልካም ብንሠራበት ከእግዚአብሔር ዘንድ መልካም የሚሆንልን አይደለምን? ጌታም "… የዓመፃ ገንዘብ ሲያልቅ በዘላለም ቤቶች እንዲቀበሏችሁ በእርሱ ወዳጆችን ለራሳችሁ አድርጉ" ሲል መክሮናል ፈፅመው የተጠቀሙበትም ብዙዎች ናቸው፡፡


 

 

የእግዚአብሔር ሕግ(ቃል)፡- የሰው ልጅ ቅድሚያ ለያስተውለው የሚገባው ዋና ነገር ቢኖር ጌታ "ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም" ብሎ ያስተላለፈው ታላቅ መልእክት ነው፡፡ መብላት መጠጣትና መራባት ሕገ እንስሳ እንጂ ሕገ ሰብእ አይደለም፡፡ ሰው ከመብላት ከመጠጣትና ከመራባት ያለፈ ዓላማ ይዞ የተፈጠረ ፍጥረት ነው፡፡ ይኸውም ዓላማ የፈጣሪውን ክብር መውረስ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በእግዚአብሔር ቃል(ሕግ) መሠላልነት የሚደርስበት ሠገነት ነው፡፡ ለሰው የእግዚአብሔር ቃል ከሥጋና ከነፍስ ደዌ የሚፈወስበት መድኃኒት፤ከሥጋዊም ሆነ ከመንፈሳዊ የጠላት ሠራዊት የሚሸሽግበት ዐለት፣ ከርኲሰቱ የሚጠራበት፣ ከድካሙ የሚበረታበት፣ ከስብራቱ የሚጠገንበት፣ከሀዘኑ የሚፅናናበት፣ከድንቁርና ጨለማ ነፃ የሚሆንበት ብርሃን ነው፡፡ ሥጋ የሚያስፈልገውን ካጣ ከስቶ  ጠውልጎ ውበቱ ደምግባቱ ተበላሽቶ እንዲታይ ነፍስም የእግዚአብሔር ቃል ከተለያት ውበት ደም ግባቷ የሆነ ንፅህና ቅድስና ጠፍቶባት ጠውልጋ ተበላሽታ ትታያለች፡፡ የሥጋ ክሳትና ጉስቁልና በዓይነ ሥጋ እንደሚታይ የነፍስ ጉስቁልና በዓይነ ልቡና ይታያል፡፡ ሰው በዝሙት፣ በሀሰት፣ በስርቆት፣በክፋት፣ በሀሜት፣በስድብ እግዚአብሔርን ባለመፍራት ሰውንም ባለማፈር ሲመላለስ እንኳን በሕገ እግዚአብሔር ፀንተው ላሉ፣ በግብር ለሚመሰሉትም ይከፋል፡፡ በሁሉም ይነወራል፡፡ የነፍስም ጉስቁልና በዚህ ይታወቃል፡፡

ለዚህ ነው ነብዩ ዳዊት " ሕጉን በቀንና በሌሊት የሚያስብ ሰው ቅጠሉ እንደማይረግፍ ፍሬዋንም በየጊዜዋ እንደምትሠጥ በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደተተከለች ዛፍ ነው" ያለው፡፡ እስኪ ለጥቂት ደቂቃ ኑሮአችንን ያለ ውኃ ለማሰብ እንሞክር፡፡ ውኃን ብናጣ ምን ሊፈጠር ይችላል? ያለውኃ ምግባችንን ማብሰል እንዳንችል፤ ያለ ቃለ እግዚአብሔርም  እርሱን ወደማወቅ ብስለት ልንደርስ አንችልም፡፡ ያለውኃ የሥጋ ንፅህናን ማግኘት እንዳንችል፤ ያለ ቃለ እግዚአብሔርም የነፍስ ንፅህና አይገኝም፡፡ ያለውኃ ቤት መስራት እንዳይቻል ያለ ቃለ እግዚአብሔርም ሰማያዊ ቤት አይኖረንም፡፡ ያለውኃ በሥጋ መኖር እንዳይቻል ያለቃለ እግዚአብሔርም ነፍስ ሕይወት የላትም፡፡ ሐዋርያት ለዚህ ነው ጌታችንን" ካንተ ወዴት እንሔዳለን አንተ የህይወት ቃል አለህ" ያሉት፡፡

   ነብዩ ዳዊት ለክብረ መንግስቱ የሚገበርለት ብዙ ብርና ወርቅ ቢኖርም ሕይወት እንደማይሆነው ከሞትም እንደማያድነው ሰለተገነዘበ ነው ሕግህ(ቃልህ) ይሻለኛል ያለው፡፡ ሰው በብር በወርቅ ከሚያጌጥ በእግዚአብሔር ሕግ ቢያጌጥ፤ በብር በወርቅ ከሚከብር በእግዚአብሔር ቃል ቢከብር ለሰውም ለእግዚአብሔርም ደስ ያሰኛል፡፡ ብዙ የምድር ባለፀጋዎች አልፈዋል ከነስም አጠራራቸውም ተረስተዋል፡፡ በእግዚአብሔር ቃል የከበሩ ግን በምድርም ሆነ በሰማያት የዘላለም መታሰቢያ ቆሞላቸዋል፡፡

-ዳዊት እንደልቤ የተባለ ስለሀብቱ ብዛት ሳይሆን እግዚአብሔርን ሰለመፍራቱና ቃሉን ስለማፍቀሩ ነው፡፡                                       -ነቢያትና ሐዋርያት ጻድቃንና ሰማዕታት የሚታወሱት በባለሟልነትም የሚታሰቡት ሕጉን ሰለጠበቁና ቃሉን ሰላገለገሉ እንጂ ስለ ብርና ወርቃቸው ብዛት አይደለም፡፡ ኢሳ 56፥1-ፍፃሜ

-ሙሴም ከእግዚአብሔር ጋር ፊት ለፊት እስኪነጋገር ድረስ በባለሟልነት የከበረ የግብፅን ገንዘብና ሹመት ስለመናቁ አይደለምን? ዕብ11፥23-28

   በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አብራችሁኝ የተስፋው ቃል ተካፋዮች የሆናችሁ ወንድሞቼና እህቶቼ ቃሉ በእኛ ቢኖር እኛም በቃሉ እንኖራለን፡፡ በትዕዛዙ የምንሔድ በቃሉም የምንኖር ከሆነ ራሱን ይገልጥልናል ይወደናልም በእኛ ዘንድም መኖርያውን ያደርጋል፡፡ ዮሐ14፥18-24

ቃሉን የማይናፍቅ ሕጉን ሲሰማ የሚሰለቸው ራሱ በፈጠረው በሚመቸው ህግ ለሚኖር ለዚያ ሰው ወዮለት፡፡ ታላቅ ፍርድ ይጠብቀዋልና፡፡ ሞት በሙስና አይታማም፡፡መማለጃም ሰጥቶትም ህይወቱን ያረዘመ ሰው ዓለም ከተፈጠረ አልሰማንም፡፡ የልዑሉን ትዕዛዝ ፍርዱንም የሚያስፈፅመው መላዕክትም በብርና በወርቅ አይደለሉም፡፡ በሲዖልም በሀብታችን የተሻለ ቦታን ልንመርጥ አይቻለንም፡፡ ያ ዓለም ብርና ወርቅ የሚሠለጥንበት ዓለም አይደለምና፡፡

ቃሉን የሚያፈቅሩ ሕጉንም የሚወዱ ግን ዝማሬያቸው ይህ ነው፡፡

ከአእላፋት ወርቅና ብር ይልቅ የአፍህ ሕግ ይሻለኛል አቤቱ ሕግህን እንደምን እጅግ ወደድሁ ቀኑን ሁሉ እርሱ ትዝታዬ ነው፡፡ ቃልህ ለጉሮሮዬ ጣፈጭ ነው ከማርና ከወለላ ይልቅ ለአፌ ጣፈጠኝ ሕግህ ለእግሬ መብራት ለመንገዴም ብርሃን ነው፡፡ መዝ 118፥1-ፍፃሜ

ስለዚህ ቃሉን የያዙ በሕጉም የሚኖሩ ግን በድል ይወጣሉ፡፡ የሲዖል ግርማም በእነርሱ ላይ ኃይል የለውም፡፡ በጽዮን ተራራ ከበጉ ጋር መኖር ዕድል ፈንታቸው ነው፡፡ እርሱ አምላካቸው እነርሱ ሕዝቦቹ ይሆናሉ፡፡ ረሃብና ጥም ፣ ደዌም ፣ጉስቁልናም፣ መገፋትና መበደልም ያቀን ሀሩርና የሌሊት ቁር አያስጨንቃቸውም፡፡ ያለፈውን ሥርዓት አሳልፎ እንደ ተስፋ ቃሉ ሁሉን አዲስ ያደርጋልና፡፡ እንደ ተስፋ ቃሉ አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር መጠበቅ ወይም ለኃላፊ ብርና ወርቅ መተናነቅ ምርጫው የራሳችን ነው፡፡ የተሻለውን ለመምረጥ ህሊና ተሰጥቶናልና፡፡ ራዕይ 7፥13-17፣ 2ጴጥ 3፥13

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

 

ቀሲስ ታምራት ውቤ

Read more...

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ