Login
Main menu

...በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ ብፁዕ ነው፡፡ መዝ ፩፡፩

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

      በክፉዎች ምክር ያልሄደ በኃጢአተኞችም መንገድ ያልቆመ በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ ብፁዕ ነው፡፡ መዝ ፩፡፩

በመዝሙረ ዳዊት የተመሰገኑ ጠባይዓትንና አካሄዶችን አመለካከቶችንና ተግባራትን “ብፁዕ” በሚል የውዳሴ ቃል እያጀበ ተቀኝቶ እናገኛለን፡፡

ብፁዕ የሚለው ቃል “በፅዐ” ከሚለው የግዕዝ ግሥ የሚወጣ ሲሆን የተደነቀ የተመሰገነ ንዑድ ክቡር የሚለውን ትርጉም ይይዛል፡፡

ከላይ በተቀመጠው ጥቅስ ክቡር ዳዊት ሦስት አንድን ሰው ወደ ጥፋት የሚወስዱ ጉዳዩችን አንስቶ ከእነርሱ በተቃራኒ የሚገኝ ቢኖር ንዑድ ክቡር ነው ይለናል፡፡

ቀዳሚው በክፉዎች ምክር ያልሄደ ብፁዕ(ምስጉን) ነው ይላል፡፡ ምክር አንድን ሰው ክፉውን ጠባይዕ እንዲተው መልካሙን ደግሞ እንዲያፀና አስነዋሪ ተግባር የበጀ መስሎት የሚኖር ካለ እንዲመለስ፤ የተወደደ ሥራ ለመሥራት መንገድ የጠፋውንም ለማመላከት የሚለገስ የፍቅር የበጎነት መግለጫ ነው፡፡ ሰው የሚመክረው የሚያፈቅረውንና የሚጠነቀቅለትን ነውና፡፡

የገንዘብ ልግስና ራቁት ይሸፍን ረሃብ ያስታግስ ይሆን እነጂ ከክፉ ጠባይ ሊመልስ አይችልም፡፡ ቀና መንገድም አያመለክትም ገንዘብ፡፡ ጊዜያዊ ምክር ግን ቀዋሚ ስጦታ ነው፡፡

በተቃራኒው ክፉ ምክር ደግሞ ሰውን በነፍስ በሥጋ በአሁኑም ሆነ በዘላለማዊው ዓለም ሊያጠፋው ይችላል፡፡የክፉ ምክር መዝገቡ ክፉ ልብ ነው፡፡ ጌታም በወንጌል ክፉ ዛፍ መልካም ፍሬ ሊያፈራ መልካም ዛፍ ክፉ ፍሬ ሊያፈራ እንደማይችል አስተምሯል፡፡ ጨምሮም ሰውን የሚያረክሱ ክፉ አሳቦች ሁሉ መዝገባቸው ክፉ ልብ መሆኑን አስረግጦ ተናግሯል ማቴ 7፤ ማቴ 15፡፡ በመሆኑም ምክር ሁሉ እንደ መካሪው ማንነት ይወሰናል፡፡ በሕይወት ጉዞ ሰው ክፉም መልካም መካሪ ሊገጥመው ቢችልም በዚያ ተምስርቶ በሚሠራው ሥራ ወይም በሚገልጠው ጠባይ የሚወደሰውም ሆነ የሚነወረው ፤የሚሸለመውም ሆነ የሚቀጣው ራሱ ነው፡፡

ንጉስ ዳዊት በቃሉ ክፉ መካሮች እነዳሉ ከገለጠ በኋላ ብፁዕ የሚባለው ግን በነዚያ ምክር ፈቅዶም ሆነ ተታሎ ያልሄደ መሆኑን አስቀምጧል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም ሆነ ታሪክ በክፉ ምክር የተጎዱ የብዙ ሰዎችን የሕይወት ተሞክሮ በዋቢነት ዘግቦ ይዟል፡፡

. የእናታችን ሔዋን በምክረ ከይሲ መመራት በራሷም ሆነ በዘሯ በመከራ ለመጎብኘታቸውና በሞት ለመዳኘታቸው ምክንያት ሆኗል፡፡ መካሪ ምክሩን የሚጀምረው ጉዳያችንን /ምሥጢራችንን/ ከመስማት ነውና በመጀመሪያ ለማን ምን መንገር እንዳለብን ማስተዋል ይገባል፡፡ ምንም እንኳ የሔዋንና የአዳም በደል/ኃጢአት/ ባህርያዊ ያይደለ በክፉ ምክር ተታለው የፈፀሙት ቢሆንም ከመቀጣት አልዳኑም፡፡ ወደ ቀደመ ክብራቸው የተመለሱ በልጅ ሞት ተክሰው መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ስለ ወላጅ በደል የልጅ ሞት ምን ያህል ይከብድ፡፡ ዛሬም እንዲሁ ነው በወላጆች ጥፋት ልጆች በቀደምት በደል ደኅርት መቀጣታቸው፡፡

ሔዋን እንደ ርዕስ ተነስቶ ምክርና ማስጠንቀቂያ ባልተሠጠበት ጉዳይ ላይ ቢሆን ኖሮ የሳተች ባልፈረድንባት ነበር፡፡ ነገር ግን መልካምነቱን የምታውቀው የአባትነት ድምፁን የለመደችው በእጁ ከመፍጠር አንስቶ ሁሉ እድትገዛ የሠጣት ጌታ እግዚአብሔር የመከራትን ምክር ማንነቱን በማታውቀው ለእርሷ ሕይወት ምንም አስተፅኦ ባልነበረው ባዕድ (እንግዳ) በአንዲት ቅፅበት ንግግር የብዙ ዓመቱን የፍቅር ግንኙነት ማቃለሏ ጭምር በብዙ ያስወቅሷታል፡፡

በመሆኑም ሲጀምር መካሪም ማን መሆኑን ሲቀጥልም ምክሩ በጉዳዩ ላይ አስቀድመን ከሰማናቸው አስተያየቶችም ሆነ ማስጠንቀቂያዎች ጋር ያለውም ተዛምዶ ወይም ተቃርኖ ፈትነን መጓዝ ከኛ የሚጠበቅ ዓይነተኛ ተግባር ነው፡፡ ሰው የሚያስበው የሚናገረው የሚወስነው የሚሰራው ወዘተ ለራሱ ብቻ አይደለም ውጤቱም በራሱ ብቻ አይቆምም፡፡ ላለፈ ትውልድ ታሪክ ለሚመጣውም ደኅንነት ትልቅ ኃላፊነት ተሸክሟል፡፡ የኛ ሕይወት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የብዙዎች ትክክለኛ ወይም የተሳሳተ አስተሳሰብ ምክር እንዲሁም ተግባር ውጤት ነው፡፡ የኛም ተጽእኖ በሌሎች ላይ እንዲሁ ነው፡፡ በእኛ የአካልም ሆነ የመንፈስ አብራክና ማህፀን ውስጥ ብዙ ልጆች ሳይሆን ትውልዶች አሉ፡፡ ዛሬ በክፉ ምክር ስተን የምንፈፅመው ተግባር በርካታ ትውልድን ዋጋ ያስከፍላል፡፡ በመልካም ምክር ተመስርተን የምንሰራው ሥራም ለትውልደ ትውልድ ጥቅም ይውላል፡፡ ብዙዎቹም ይታነፁበታል፡፡ ስለነቢዩ ዳዊት ልጆችም እንዲህ ተጻፈ፡፡

ለ. የንጉስ ዳዊት የበኩር ልጅ አምኖን በአባቱ በኩል እህቱ የሆነችውን ትዕማርን በማፍቀሩ ምክንያት ትካዜ በዛበት፡፡ እህል የማይበላ ከመሰሎቹም ጋር የማይጫወት ስሜቱን እያሰታመመ የሚቆዝም ሆነ፡፡ ይህን የተመለከተ ኢዮናዳብ የተባለ ጓደኛውም የንጉሱ ልጅ በምን ምክንያት ደስታ እንደራቀው በጠየቀው ጊዜ በውስጡ ያለውን እረፍት የነሳውን ስሜቱን ተረከለት፡፡ የኢዩናዳብ ምክርም “ታምሜያለሁ ብለህ ተኛ ንጉሱ ልጆቹን ይወዳልና ሊያይህ ይመጣል በዛን ጊዜ ትዕማር ከእጇ እንድበላ ወደኔ ትመጣ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን ብለህ ጠይቀው በዛን ጊዜ የወደድከውን ትፈፅማለህ” የሚል ነበር፡፡ አምኖን እንደተመከረው አደረገ ትዕማርም ባባቷ በንጉስ ዳዊት ወንደምሽ ታሟልና ተንከባከቢው የሚል መልእክት ደረሳት፡፡ ትዕማር የሚበላው ልታቀርብለት ወደ እልፍኙ ስትገባ ከእርሱ ጋር ትተኛ ዘንደ ግድ አላት ትዕማር “ወንድሜ ሆይ አይሆንም እንዲህ ያለ ነገር በእስራኤል ዘንድ አይገባም እና አታሳፍረኝ ይህን ነውረኛ ሥራ አታድርግ እኔም ነውሬን ወዴት ልሸከም? አንተም በእስራኤል ዘንድ ከምናምቴዎች እንዳንዱ ትሆናለህ፡፡ እንግዲህስ ለንጉሱ ንገረው እኔንም አይነሳህም ” 2ሳሙ 13፡1-ፍፃሜ በማለት የመከረችውን አልሰማትም፡፡ ከክብር አሳነሳት የንጉስ ዳዊትን፣ የራሱን፣ የትዕማርና ባጠቃላይ ለቤተሰቡና ለእስራኤል ኃፍረት የሆነ ነውርን ፈፀመ፡፡ በዚህ ሳያበቃ ወትሮም ዝሙት በፍቅር ለምድ ተጀቡና ቀርባው ነበርና ሲያልፍለት ከቀደመው የከፋ በደል ፈጸመ፡፡ መጽሐፍ አምኖን ትዕማርን “ቀድሞ ከወደዳት ውድ ይልቅ ኋላ የጠላት ጥል በለጠ” እንዲል በጉልበት ካስነወራት ከክብርም ካሳነሳት በኋላ በታላቅ ውርደት ከቤቱ አስወጥቶ አባረራት፡፡

ክርስቲያኖች የዝሙት መልኳ እነሆ ይህን ይመስላል፡፡ ፊት ታጣድፋለች መብልና እንቅልፍ በመንሳት እረፍት አሳጥጣ ታስጨንቃለች፡፡ ኅሊናችን በትክክል እንዳያስብ በስሜት ግርዶሽ ታጨልመዋለች፡፡ በዚህ ላይ ለዝሙት የሚያበረታታ የሚፋፋ ክፉ መካሪ ሲያጋጥም መጨረሻዋ መራር ይሆናል፡፡

በዝሙት በተወጠረ ኅሊና ዘንድ ፍቅር አትታወቅም፣ትዕግስትም ሥፍራ የላትም፣ራስን መግዛት ምውት ናት፡፡ በመተቃቀፍ ውስጥ ፍቅር የለችም ጊዜያዊ ስሜት እንጂ፡፡ አንዱን የእንዱን አካል ማክበር አይታሰብም ተራ መጠቀሚያ አድርጎ ከመቁጠር በቀር፡፡

እህቶች ሆይ በክፉ ኅሊና ከሚያደባ በልዝብ ምላስ ከሚሸነግል በመጎምዥት ዓይን ከሚያይ ተጠንቀቁ፡፡ በማን እልፍኝ እንደተገኛችኁም አስተውሉ፡፡

ትዕማር በንፅህና ሙሽራዋን የምትጠብቅ የክርስቲያን ነፍስ ትወክላለች፡፡ ድንግልና በሥጋ ላለ ንጽህና ማሳያ ነውና፡፡ አምኖን የዓለም ምሳሌ ነው፡፡ ይህች ዓለም እኛን በሥጋ ፍቃድ አጥምዳ በኃጢአት እስክትጥለን ድረስ ዕረፍት የላትም ክብራችንን ከጣልን በኋላ ግን ትከፋብናለች፡፡ ኢዩናዳብ የዲያብሎስ ምሳሌ ነው የዚህ ሁሉ ሴራ አቀናባሪ ነውና፡፡ በዓለም ከሚሠራው ኃጢአት፣ተንኰል፣ክፋት፣ዝሙት፣ጥላቻ መከዳዳት ወዘተ…ጀርባ ያለው ክፉው የዲያብሎስ ምክር መሆኑ የታወቀ ነው፡፡

ብዙዎች ወደ ዓለም እልፍኝ በክብር ገብተው በውርደት፤በሳቅ ገብተው በለቅሶ፤በዕልልታ ገብተው በዋይታ፤በሙላት ገብተው በጉድለት ወጥተዋል፡፡ አምኖን “እኅቴ” እያለ ይነጋገራት እንዳልነበር ፈቃዱን ከፈጸመ በኋላ “ይህቺን ሴት ከፊቴ አስወጥተህ በሩን ዝጋባት” በማለት ጭካኔውን ገልጿል፡፡ ዲያብሎስ ማንንም በክቡር ማማ ላይ ሲያወጣ በመልካም ሲያነጋግር ለእኔ ካለው ፍቅር የተነሳ ነው ብሎ ካሰበ የመጨረሻው የሞኝነት እርከን ላይ መቆሙን ይወቅ፡፡ ከዝንብ ማር እንደማይገኝ ከዲያብሎስም ርኅራኄን አትጠብቅ፡፡እርሱ ፍቅርን ማወቅም መፈጸምም የሚሻ ፍጥረት አይደለም፡፡

ትዕማርም የንጉስ ልጆች ደናግላኑ የሚለብሱትን ብዙ ኅብር ያለውን ልብሷን ቀዳ በራሷ ላይ አመድ ነስንሳ እጅዋንም ራሷ ላይ ጭና እያለቀሰች ሄደች፡፡

በብዙ ኅብር ያጌጠ ልብስ የተባለ በብዙ ሀብታት(ጸጋዎች) የከበረ በንጉስ ልጅ ማዕረግ የተደነቀ ተፈጥሯችንን ያመለክታል፡፡ በክፉ ምክር ግን ይህ ሁሉ ይጠፋል፡፡

ትዕማር በወንድሟ በአቤሴሎም ቤት መበለት ሆና ተቀመጠች አምኖንም ከሁለት ዓመት በኋላ በአበሴሎም የቂም ሰይፍ ክፉ አሟሟት ሞተ፡፡

. አምኖን በእህቱ ላይ በሠራው በደል የተበቀለው አቤሴሎም በተራው እስራኤል በተሰበሰቡት በፀሐይ ፊት አባቱ ንጉስ ዳዊትን ለማዋረድ ከአባቱ ቁባቶች ጋር ተኛ፡፡ ይህን ታላቅ ኃጢአት ያለ ኃፍረት ይፈጸም ዘንድ ያነሳሳው ክፉ መካሪው አኪጦፌል ነበር፡፡ እርሱም በተራው ክፉ አሟሟት መጨረሻው ሆነ፡፡

እኒህ ሁሉ ታሪኮች የሚያሳዩን በክፉዎች ምክር መሄድ ለገሚሱ የሕይወት ምሬት ለተከታዩም መራር ፍጻሜ እንደሚያስተከትል ነው፡፡

ክቡር ዳዊት ንጉሱ ሳኦል ነፍሱን ሲሻ ካንዴም ሁለቴ ለመግደል የሚያሰችለው አጋጣሚ ቢመቻችለትና ዙራውያውን ያሉ መካሪዎችም እጁን እንዲያነሳ ቢጎተጉቱትም “እግዚአብሔር በቀባው ላይ እጄንን አላነሳም እንደ ቅንነቴ ይመልስልኛል” በማለት ክፉ ምክራቸውን አልተቀበለም በዚህም “እንደ ልቤ” እስከ መባል በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስ አግኝቷል፡፡

ማጠቃለያ፡- ምክር ሰምቶ ለሚፈጽማት መልካም መሆኗ አሌ የማይባል ሀቅ ቢሆንም የምክሩን ዓይነት ግን ከእነዚህ ሕግጋት ጋር የማይጣረስ መሆኑን ማስተዋል ያሰፈልጋል፡፡

፩. የተፈጥሮ ሕግ፡- የተደነቀው ተፈጥሯችን ያለ ሕግ አልተሠራም፡፡ በዙሪያው ካሉ ሌሎች ፍጡራን ጋር በኅብረት እንዲኖር የሚያደርገው የመደጋገፍና የድኅንነት ሕገጋት አሉ፡፡ በአጠቃለይ በግላዊ ተፈጥሯችን ላይም ሆነ ከሌሎች ጋር በሚያስተሳስረን የተፈጥሮ ቀመር ጋር የሚጋጭ ምክርና ተግባር በዚህ ምድር ያለንን ቆይታ ያዛባዋል፡፡ ተፈጥሮን በሠራት ዘንድን ያስጠይቀናል፡፡ ዛሬ በሥልጣኔ ወይም በነጻነት ስም ከተፈጥሮ ባህርይ ውጪ የሚፈጸሙ ብዙ አስነዋሪ ተግባራት እንደ መልካም የመብት ጥያቄ በየመድረኩ ሲነሱና የወራዙትን ሕሊና በሚማርክ መልኩ ሲቀርቡ ይታያል፡፡ ዘመናዊው ሚዲያ የማኅበረሱቡን የሥነ-ምግባር ዕሴቶች ጠብቆ የማቆየትና ለትውልድ የማስተላለፍ ሚናውን ዘንግቶ ንግድ ላይ ያተኮረ በመሆኑም ለወጣቶቹ ሕይወት ኃላፊነት በጎደለው መልኩ ተቀርጿል፡፡ ዛሬ ዋጋ እያሰከፈለን ያለው የዚህ ሁል ድምር ውጤት ነው፡፡

፪. የማኅበረሰብ ሕግ፡- ማንኘውም ሰው ማንነቱ ተቀርፆ የሚመጣው በዚህ እንደመሆኑ መጠን ይህንኑ የመጠበቅና ግዴታ ይኖርበታል፡፡ ከማኅበረሰብ መገለል ወይም አንደ ሥርዓት አልባ መቆጠር ከዚህ በተቃራኒው ከመሆን  የሚመጣ ነው፡፡

. አምላካዊ ሕግ፡ የተፈጥሮም ሆነ የማኅበረስብ  ሕግ ወይም ሌላ ሕገጋት መነሻቸው አምላካዊ ሕግ ነው፡፡ እንደ ክርስቲያን የምንሰማው ምክር ሁሉ የሚመዘነው ከዚህ አንፀር ነው፡፡ ከአምላካዊው ሕግ በተቃራኒ የሚቀርብ ምንጩ ከክፉ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ የአምላክ ሕግ የአምላክ ምክር ለሁሉ እርምጃችን ሚዛን ነው፡፡

ሰው ይህንን ሁሉ በማስተዋል በክፉዎች ምክር ከመጓዝ ቢቆጠብ በሥጋውም ሆነ በነፍሱ ደኅንነቱ በዙሪያው ላሉ መሰሎቹና በተፈጥሮ ለሚዛመዱት ሁሉ የደስታና የሰላም ምንጭ ይሆናል፡፡ ትናንትን በፀፀት ዛሬን በኃፍረትና በንዴት ነገንም በፍርሃት የሚያስተናግድ ሕይወትም አይኖረውም፡፡ ስኬታማ ሕይወት ይሏል ይህ ነው፡፡

ይቆየን

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቀሲስ ታምራት ውቤ

 

ሕዳር ፳፻፮ ዓ.ም

Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ