Login
Main menu

ኒቆዲሞስ

Index

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ኒቆዲሞስ፡- ጌታችን ኒቆዲሞስ ከሚባል የአይሁድ መምህር ጋር የነበረውን ቆይታ የምናስብበት ሰንበት ነው፡፡

ምስባክ፡- ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ

        አመከርከኒ ወኢተረክበ ዓመጻ በላዕሌየ

        ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ ዕጓለእመሕያው፡፡

ትርጉም፡- ልቤን ፈተንኸው በሌሊትም ጐበኘኸኝ

        ፈተንኸኝ ዓመፃም አላገኘህብኝም

        የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው፡፡

- ክቡር ዳዊት ከንጉሡ ሳዖል ጋር በነበረው ጠብ የተናገረው ነው፡፡ ምንም እንኳ ሳዖል ቢከፋብኝም ካንዴም ሁለቴ በእጄ ጥለኽው ፈተንኸኝ፡፡ እኔ ግን እንደሆነብኝ ልሁንበት እንዳደረገብኝ ላድርግበት የሚል ክፋትን፣ ቂም፣ በቀልን በልቤ አላገኘኸብኝም፡፡ በአፌም እግዚአብሔር በቀባው ላይ እጄን አላነሣም ከማለት በቀር ጠላትህን በእጅህ ጥሎልሃል ከሚሉ ጋር ተባብሬ አልተገኘሁም ሲል ነው፡፡

         ዳዊት ምን ያህል የዋህና ኃዳጌ በቀል መሆኑን መጽሐፍ “ዳዊት ከሳዖል ልብስ ዘርፉን በመቁረጡ አዘነ” ተብሎ ተጽፏል፡፡ የስንት ወንድሙን አንገት በሰይፍ፣ የስንት ወገኑን አንጀት በረሃብ፣ የስንት ባልንጀራውን ተስፋ የተሞላ ሕይወት በመድኃኒት፣ስንቱን ትዳር በነገር ቆርጦ ሲጥል ቅንጣት የማይሠማው ጨካኝ በሞላበት ዓለም እንዲህ ዓይነት ልብ እንደምን ያለ ነው?

          ሊገድለው ሠራዊት አስከትሎ የወጣ በተደጋጋሚ ጦር ወርውሮ የሳተ ለመግደል ቁርጥ ህሊና ያለው ጠላት ላይ የማይጨክን ክንድ እንዴት የተባረከ ነው? በዚህ ዓለም ስንቱ በጠላቱ ያይደለ በወዳጁ፣ በባዕድ ያይደለ በዘመዱ፣በመጻተኛ ያይደለ በወገኑ ላይ ግፍ ሠራ፡፡ ዳቦ ሲጠብቅ ድንጋይ፣ ዓሣ ሲለምን እባብ አቀረበለት፡፡

         ቅዱስ እግዚአብሔር ማዕምረ ኅቡዓት ልብ የሠወረውን ኩላሊት የሸሸገውን ሁሉ የሚያውቅ ከኅሊና አስቀድሞ የሚመረምር ከሀሳብ አስቀድሞ የሚፈትን ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ሰው ከሰው ተሠውሮ እንዲሠራ አይደለም፡፡ጽድቃችን ይሁን ኃጢአታችን፣ነውራችን ይሁን ክብራችን በፊቱ የተገለጠ ነው፡፡ የቦታ ርቀት የጨለማ ጽናት ልዑሉን አይጋርደውም፡፡ ሁሉን ያያል ሁሉን ያውቃል ሁሉን ይመረምራል፡፡ ኪዳን ዘነግህ

         የያዕቆብ ልጅ ዮሴፍ “በእግዚአብሔር ፊት እንዴት ኃጢአትን እሠራለሁ” ያለ በግብፅም ምድር ሆነ በከነዓን የእግዚአብሔር ዓይኖች የተገለጡ መሆናቸውን በማወቁ ነው፡፡ በፍትወት ተቃጥላ በኃጢአት ሠክራ የነበረች የጲጥፋራ ሚስት ግን ይህን ማስተዋል የምትችልበት ሁኔታ ውስጥ አልነበረችም፡፡ዘፍ 39፥7-11

        ሰው ኅሊናው በፍትወት ሲሸነፍ በኃጢአት ፍቅር ሲማረክ ጌታ እግዚአብሔር በሁሉ የሚገኝ መሆኑን ለማየት አዕምሮው ይጨልማል፡፡ ቅዱስ አምላኩን በሥራ ለመካድ ደግሞ የሚመርጠው ጨለማን ነው፡፡ ይህም ኅሊናው ከእግዚአብሔር በመለየቱ የወደቀበትን ጨለማ ያሳያል፡፡ ጌታም “ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፤ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም” በማለት ኃጢአትንና ክፉ ሥራን የሚወዱ ከጨለማ ጋር ያላቸውን ዝምድና አስታውቋል፡፡ ዮሐ3፥20

        ህፃናት ጥፋት ሠርተው የሚቀጡ መሆናቸውን ሲያውቁ ከቤተሰብ ይደበቃሉ፡፡ሲደበቁ በዋናነት የሚሠውሩት ከሌላው ሰውነታቸው ይልቅ ፊታቸውን ነው፡፡ በእነርሱ የአስተሳሰብ ደረጃ እነርሱ የማያዩት ሁሉ ሊያያቸው አይችልም፡፡ ልብ ያለው ልብ ይበል፡፡

        ነቢዩ ዳዊት ግን “ዓይንን የፈጠረ አያይምን ጆሮንስ የፈጠረ አይሰማምን…” በማለት ልዑሉን ይገልፀዋል፡፡ በእኛ አነጋገር ምክንያታዊ በሆነ መንገድ፡፡ መዝ 93፥7-10 በቅዳሴም “እግዚአብሔር ያያል ልቡናችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ” በማለት ማወጁ ወደ ኅሊናችን እንድንመለስ አይደለምን? ቅዳሴ እግዚእ ቁ.፲፫

ስለ ኒቆዲሞስም “በሌሊት ፈተንኸኝ ዓመፃም አላገኘህብኝም” ማለቱ ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ በሌሊት ሲመጣ ሁሉን በሚያውቅ በእርሱ ፊት በተንኮል እንዳልቀረበ ያጠይቃል፡፡ ኒቆዲሞስ በሌሊት ወደጌታ የሄደ በተንኰል ሊያጠምደው ወይም እንደ ሌሎቹ ረበናተ አይሁድ በጥያቄ ሊፈትነው አልነበረም፡፡ የእስራኤል መጽናናት በእርግጥ ጊዜው እንደደረሰ ለማወቅ እንጂ፡፡

እንደሌሎችም “ይህ የጸራቢው የዮሴፍ ልጅ አይደለምን? የሚል ቃል በአንደበቴ እናገር ዘንድ አልወደድሁም፡፡ ይልቁን “… እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን በማለት ከመመስከር በቀር፡፡ አመጣጡ መልካም ስለነበር ጌታችን ታላቅ የሆነ ከእግዚአብሔር ልጅነት የሚገኝበትን ምሥጢር ገልፆለታል፡፡ ዮሐ 3


More in this category: « ገብር ሔር ሆሣዕና »

Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ