Login
Main menu

ጰራቅሊጦስ

Index

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን!

ጰራቅሊጦስ የሚለው ቃል የጽርዕ ሲሆን ‹‹የቅርብ ረዳት፤በአጠገብ ሆኖ የሚያፅናና የሚያረጋጋ›› የሚለውን ትርጉም ይሰጣል፡፡ይህ መጠሪያ በመጽሐፍ ቅዱስ ጌታ መንፈስ ቅዱስ ከተጠራባቸው ስሞች አንዱ ነው፡፡

     ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ለዓለም ከገለጠና ምሥጢረ መንግሥትን ሦስት ዓመት ለሐዋርያት ሲያስተምር ከቆየ በኋላ ጊዜው እንደደረሰ አውቆ ለሐዋርያት ከእነርሱ ተለይቶ እንደሚሔድ ነግሯቸው ነበር፡፡ በእርግጥ ሐዋርያት ተላልፎ የመሠጠቱንና የሞቱን ነገር ደጋግመው ሲሰሙት የነበረ ቢሆንም የተቆረጠው ቀን መድረሱን ሲረዱ ግን ከፍተኛ ድንጋጤ ወደቀባቸው፡፡

     በዚህ ጊዜ ነው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ እሔዳለሁ ስላችሁ ደስ ሊላችሁ ይገባል፤እኔ ካልሔድኩ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና ያላቸው፡፡ ጌታችን የሐዋርያትን መደንገጥ ማዘንና መሸበር ሲያይ መንፈስ ቅዱስ ወደ እነርሱ የሚመጣው ሊያረጋጋቸውና ሊጽናናቸው መሆኑን አብስሯቸዋል፡፡ ያድርባችኋል በውስጣችሁም ይኖራል እርሱም ዓለም ሊቀበለውና ሊያውቀው የማይችል የእውነት መንፈስ ነው በማለትም አስረድቷቸዋል፡፡

     የክብር ጌታ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ነሥቶ ከተነሳ በኋላ

በ$ኛው ቀን ሲያርግ ‹‹አብ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ›› በማለት ተስፋን ሰጥቷቸው ሄዷል፡፡ ከአሥር ቀን በኋላም እንደ ቃሉ ተፈጽሟል፡፡ ሉቃ 24፥49

     መጀመሪያ በሐዋርያት ለጥቆም በምዕመናን ላይ መንፈስ ቅዱስ አደረባቸው ስንል ሀብቱ ጸጋው ኃይሉ ማለታችን እንጂ በአካል በእነርሱ አደረ ለማለት አይደለም፡፡ያደረባቸው ሰዎች በሚያሠራቸው ሥራ ተገልጠው ይታወቃሉ፡፡ መንፈስ ቅዱስየሚሠራው ሥራ የሚሰጠውም ኋይልና ጸጋ በዓለም ባለ የትኛውም ጥበብ፣ ሀብትና ሥልጣን ሊገኝ(ሊሠራ) ፈጽሞ የማይችል ነው፡፡

     ጌታ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ባደረባቸው ጊዜ ከብልየት ታደሱ በአዕምሮ ጎለመሱ፤ ፍሩሃን የነበሩ ጥቡዓን ሆኑ፡፡አንዲት ቋንቋ ብቻ ይናገሩ የነበሩ  ፸፩ቋንቋ ገለጠላቸው፡፡ መተርጉማን ስለምን ቋንቋው ፸፪ሆነቢሉ በጊዜው በዓለም ይነገር የነበረ ቋንቋ(ልሳን) ይኸው ነበርና ለዓለም ሁሉ ወንጌል መንግሥትን ይገልጡ ዘንድ ፈቃዱ መሆኑን ሊያጠይቅ ነው ይላሉ፡፡ የሐዋ.ሥራ 2፥1-ፍጻሜ

     ከዚህም በተጨማሪ መጻሕፍትን ከገበታ እስከ ገበታ አወቁ ምሥጢር ተገለጠላቸው፤ ትንቢተ ነቢያትን እነርሳቸውን መስለውና ተካክለው ተረዷቸው ተረጎሟቸው አመሰጠሯቸው፡፡ጌታችን የትምህርታቸውን(የቃላቸውን)ደገኛነትም በሚከተሏቸው የተለያዩ ምልክቶች አጸናላቸው፡፡ ያመኑትን ድውያንን ፈወሱ ሙታንን አነሱ፡፡ለወንጌል እንቅፋት የሆኑባቸውን በተግሳጽ በመቅሰፍት ከመንገድ አስወገዱ፡፡ እንግዲህ ይህ ሁሉ ሀብት ጸጋና ኃይል በየትኛውም ምድራዊ ኃይል፣ ሥልጣን፣ጥበብና ብልጥግና ሊገኝ የማይችል ከላይ(ከአርያም)ለመሆኑ ማረጋገጫ ነው፡፡ ማር 16፥17፤የሐዋ.ሥራ 3-6፤የሐዋ.ሥራ 13፥7-12

     ለመግቢያ ያህል ይህን ካልን ጰራቅሊጦስ ማለት ምን ማለት ነው የሚለውን በዝርዝር ለማየት እንሞክራለን፡፡ ጰራቅሊጦስ ማለት፡-

1. መጽንዒ ወይም የሚያጸና ማለት ነው፡፡ሐዋርያት ወንጌል መንግሥትን ለመስበክ የወጡት መልእክታቸውን አሜን ወአሜን ብሎ ለመቀበል በናፍቆት ወደ ሚጠብቅ ሕዝብ አይደለም፡፡ ይልቁንም በጥላቻ በተመረዙ አይሁድና በጣዖት አምልኮ በደነዘዙ አሕዛብ መካከል ነው፡፡

     የክርስትና አስተምህሮ በወቅቱ ከነበረው የዓለም ኅብረተሰብ ባህልና አኗኗር ጋር የብርሃንና የጨለማ ያህል መራራቅ ነበረው፡፡በመሆኑም አይሁድን ሥርዓተ ኦሪትን አሕዛብን ልማደ ጣዖትን ለማስጣል ሲወጡ ብዙ ግፍንና መከራን ተቀብለዋል፡፡ጌታችን እንዳላቸው ኃይልን ሳይቀበሉ ለስብከት ወጥተው ቢሆን ኖሮ መንፈስ ቅዱስ ባላደረበት ሰውነታቸው መከራ ቢያጸኑባቸው ፈጥነው ይክዱ ነበር፡፡ስለዚህ የሚመጣውን ለመቀበል መጨከን እንዲችሉ የሚያጸና መንፈስ ቅዱስ አድሮባቸዋል፡፡

     አበው መንፈስ ቅዱስ ስለምን በእሳት አምሳል ታያቸው የሚለውን ሲተረጉሙ፤በእሳት የተቃጠለ(እሳት የነካው)መሬት ለአዝርዕት ለአትክልት እንዲመች መንፈስ ቅዱስ ያደረበትም ሰውነት ለገድል ለትሩፋት የተመቸ ነው፡፡አንድም ሸክላ ሠሪ ሸክላ ሠርታ በእሳት ተኩሳ እንደምታጸናው መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰውነት ለገድል ለትሩፋት ጽኑ ነውና ይላሉ፡፡

     መንፈስ ቅዱስ ባያድርባቸው ኖሮ ነቢያት በትንቢት ሐዋርያት በስብከት፣ሰማዕታት በደም ጻድቃን በገዳም ፀንተው ለመገኘት ባልተቻላቸውም ነበር፡፡

2. መንጽሒ፡-የሚያነጻ ማለት ነው፡፡ሰው ኃጢአት ሢሠራ የእግዚአብሔርን ልጅ የሚመስለው መልኩ ይበላሻል ባህርዩ የጎሰቁላል ጠባዩም ያድፋል፡፡በሠራነው ተጸጽተን ንስሐ ገብተንና በካህኑ የተሰጠንን ቅኖና ፈጽመን ካህኑ ከሚያደርሰው ጸሎት ጀምሮ የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እስከ መቀበል ድረስ የኃጢአት ሥርየታችን የሚከናወነው በግብረ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

እሳት ብረት ቢሉ ዝገቱን ወርቅ ቢሉ ዕድፉን አስወግዶ የቀደመ የተፈጥሮ ባህርያቸውን እንደሚያሲዛቸው እኛም በኃጢአት ምክንያት የጠፋ መልካችን ያደፈ ጠባያችን የጎሰቆለ ባህርያችን ነጽቶና ታድሶ ወደ ክቡር(ማንነቱ)የሚመለስ በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

     እመቤታችን በተለየ አካሉ አግዚአብሔር ወልድን ጸንሳ ለመውለድ እንድትችል ጥንት በአበው ባሕሪይ በማዕከል በማኅፀነ ሐና ኋላም በሕልውና ሳለች ንፅህት አድርጎ የጠበቃት ያዘጋጃት ያበቃት መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ያነጻ የከፈለ ያዋሀደ መንፈስ ቅዱስ ነው እንዲሉ ሊቃውንት፡፡

3. ናዛዚ፡- የሚያፅናና ማለት ነው፡፡ በዚህ መከራ በበዛበት ዓለም በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመንና በመልካም ሥራ በመትጋት በአብ ኅሊና ታስበው ያሉት በዚህ ዓለም በሚደርስባቸው መከራሲያዝኑና ሲተክዙ የሚያፅናናቸው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

     በመግቢያው እንዳየነው የሚያጽናና ስንል የቅርብ ረዳት የመንገዳችን ደጋፊ የነፍሳችንን ሲቃ አዳማጭ የማይለይ ታዳጊ ማለታችን እንጂ ተራ ደርሶ ሒያጅ አጽናኝ ማለት አይደለም፡፡በዓለም የሚወድቅብንን ሀዘንና ሰቆቃ ሁሉ ድል አንድንነሳው የሚያደርገን እርሱ የቅርብ አረጋጊ አጽናኛችን በመሆኑ ነው፡፡

     የቅዱሳን ሀዘን ራበኝ ጠማኝ ሀብት ንብረት ጠፋብኝ ወረት አነሰኝ ዘመድ ወገን ሞተብኝ ብለው አይደለም፡፡ ፍትሕ ሲጓደል ድሃ ሲበደል፤ እውነት ስትኮስስ ሀሰት ሲነግስ፤ የአዳም ዘር ፍርድ እንዳለ ዘንግቶ በኃጢአት በበደል ሲረክስ፤ ጻድቃንሲበደሉ ኃጥአን በምቾት በቅንጦት ሲደላደሉ ሲያዩ አምርረው ያዝናሉ፡፡ይልቁንም በቤተ እግዚአብሔር እውነተኞች መምህራን በግፍ ሲባረሩ መናፍቃንና ለመንጋው የማይራሩ ምንደኞች ሲከበሩ አምልኮተ እግዚአብሔር ሲጣስ ሥርዓት ሲፈርስ፤ ከጽድቅ ይልቅ የግብዝነት ካባ ሲደረብ ሲመለከቱ ልባቸው በሀዘን ነፍሳቸው በምሬት ይቆስላል፡፡

     በዚህ ጊዜ ጌታ መንፈስ ቅዱስ በማይመረመር ፍርዱ የደሀን ደም ሲበቀል ፍትሕን ሲተክል፤እውነትን ሲያነግስና ሀሰትን ሲደመስስ፤ በኃጢአት የከበሩ ሲዋረዱ ስለጽድቅ የተዋረዱት ሲከብሩ ፤ በኃጢአት በክህደት የተያዘውንም ሕዝብ በመጽሐፍት በመምህራን አንደበት መክሮና አስተምሮ ሲመልስ፤ በቤቱም እውነተኞቹን መምህራን አስነስቶ መናፍቃንና ምንደኞን ለይቶ አውጥቶ ሥርዓትንሲመልስ አምልኮተ እግዚአብሔር በግብዝነት ሳይሆን በእውነትና በመንፈስ ሲሆን ሲመለከቱ የቅዱሳን ልባቸው ይታደሳል ነፍሳቸው ይጽናናል፡፡ ይህም በዘመናት ሁሉ የታየ በቅዱሳት መጻሕፍትም ሆነ በታሪክ መጻሕፍት የተዘገበ ነው፡፡በፍርዱ ቅዱሳንን ያጽናናል ግፈኞችን ደግሞ እንደሥራቸው ጽዋቸውን ይግታቸዋል፡፡ የእመቤታችንንና የሐና እመ ሳሙኤልን ጸሎት ልብ ይሏል፡፡ ሉቃ 1፥46-ፍጻሜ፤ 1ኛ ሳሙ 2፥1-10

 


Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ