ጰራቅሊጦስ
4. አራኃዊየሚከፍትማለት ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ ካልሆነ በቀር ኢየሱስን ጌታ(የሕያው እግዚብሔር ልጅ፤አምላክ ወልደ አምላክ ሊል የሚችል የለም፤ እንዳለ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ የተገለጠ እርሱን ዓለማትን ካለመኖር ወደ መኖር የመጣ መጀመሪያውና መጨረሻው የሆነ አምላክ ብሎ ማመን በመንፈስ ቅዱስ ካልሆነ ከባድ ነው፡፡ 1ኛ ቆሮ 12፥3
የተመሰገነው ሐዋርያ‹‹በወንጌል አላፍርም››ማለት ወረደ ተወለደ እንደ ሰው ተመላለሰ፤ ተገረፈ ተሰቀለ ሞተ ተነሳ ዐረገ ብዬ በማመንና በማስተማር አላፍርም ያለ ለዚህ ነው፡፡ሰዎች አምላክ ብለው በኅሊናቸው የሳሉትና የጌታችን ትሑት ሆኖ በመካከላችን መገለጥ በቀላሉ ለመቀበል የሚቸግር ነውና፡፡ ሮሜ 1፥16
በሐዋርያት ሥራ ሐር ሻጭዋ ልድያ ሰለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ጳውሎስ የሚናገረውን ታዳምጥ ዘንድ ጌታ ልብዋን ከፈተላት ተብሎ የተጻፈ ለዚህ ነው፡፡ የሐዋ. ሥራ 16÷14-15 የእግዚአብሄርን ቃል ሰምተን መንፈሳዊ ፍሬ የማይታይብን ከሆነ ምክንያቱ የልብ አለመከፈት ነው፡፡ ቃሉን ሲሰማ ልቡ የተከፈተ ሰው ወዲያው ምን ላድርግ ብሎ ይጠይቃል ለንስሐም ቀጠሮ አይሰጥም ወደ ጥንት ኑሮውም አይመለስም፡፡
መንፈሳዊ ሥራን ለመሥራት ወንጌልንም ለመስበክ ጽኑ መሻታችንን ዓይቶ ሁሉን የሚያመቻች ማሕየዊ(ሕይወትን የሚሰጥ) መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡በራዕይ ‹‹ሥራህን አውቃለሁ እነሆ በአንተ ፊት የተከፈተ በር ሰጥቼአለሁ ማንምም ሊዘጋው አይችልም›› በማለት በፍልድልፍያ ላለች ቤተክርስቲያን አለቃ ታላቃ የወንጌል ሥራ ከፊቱ እንዳኖረለት የነገረው የልብ መሻትን አይቶ ሁሉን የሚያመቻች እርሱ ስለሆነ ነው፡፡ ራዕ 3፥7-8
5. መስተፍሥሒ ማለት ደስ የሚያሰኝ ደስታን የሚመላ ማለት ነው፡፡ደስታ ከመንፈስ ፍሬዎች አንዱ ነው፡፡ይህ የመንፈስ ቅዱስ ደስታ በመብልና በመጠጥ በመሾምና በመሸለም እንደሚገኘው ዓይነት ጊዜያዊ ደስታ ወይም በኃጢአት የሚሆን ፍርድና ሀዘን የሚከተለው ደስታ አይደለም፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ደስታ ማለት እግዚአብሔርን በመፈለግና በመከተል፤በቅድስናው ሥፍራ ተገኝቶ በእምነት በእውነት ሆኖ በማምለክ በመድኀኒታችን የማዳን ሥራ፤ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ከእግዚአብሔር ጋር በሚኖረን ትርጉም ያለው ግንኙነት፤ ወንጌል ሲሰበክና ሰዎች ወደ ድኅነት ሲቀርቡ ወዘተ. . .እኒህንና እኒህን በመሳሰሉት ነው፡፡ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሥጢረ መንግስተ ሰማያት አዋቂዎች ነን በሚሉ ጻፎችና ፈሪሳዊያን ሳይታወቅ በመንፈሳቸው እንደሕጻናት የዋህ ለሆኑ ሐዋርያት ስለተገለጸላቸው. . . በመንፈስ ቅዱስ ሐሴት አደረገ ተብሎ ተጽፏል፡፡ ሉቃ 10፥21
ሌላው መሐሪና ይቅር ባይ፤ ስመ ድኅነትና ስመ ሥርዓት ስለሆነው ስሙ መከራን ለመቀበል የተገቡ ሆነው ስለተገኙ ሐዋርያት ሐሴት ያደርጉ ነበር፤ደስታ ይሉሀል በሰማዕትነት ሥቃይ ውስጥ ሆነን ራሳችንን ለክርስቶስ አሳልፈን በመስጠታችንና ከእርሱ ጋር ለመሞት ስለተመረጥን የሚሰማን ደስታ ነው፡፡ በዚህ ዓለም በመንፈስ ቅዱስ ሀሴት ስለማድረግ ካሰብን ከዚህ የሚበልጥ ደስታ የለም፡፡ ለዚህ ሁሉ የሚያዘጋጅ የሚያበቃ በዓለም ከሚሆን ደስታም የሚለይ ስለሆነ ነው ጌታ መንፈስ ቅዱስ መስተፍሥሂ የተባለው፡፡ ማቴ 5፥11-12፤የሐዋ.ሥራ 5፥40-42
አንድም በዚህ ዓለም ያለን መከራ አልፈን በሃይማኖት ጸንተን በትሩፋት ሥራ ከብረን ከሥጋ ርስት ስንለይ በዘላለም ቤት የዚህን ዓለም መከራ እስክንረሳ በሚያደርስ ደስታ ያኖረናል መስተፈስሂ ይባላል፡፡ ራዕ 14፥13፤ሮሜ 8፥18
6. ከሣቲ፡-ሕይወትን የሚሰጥ ጌታ መንፈስ ቅዱስ በሕይወታቸው ደስ ለሚያሰኙት ወዳጆቹ ብዙ ነገር የተለያየ ምሥጢርን እንደየዐቅማቸው ይገልጥላቸዋል፡፡ ከቀድሞ ጀምሮ አካላዊ ቃል ዓለምን ለማዳን ከድንግል እንደሚወለድ ለነቢያት የገለጠ በእነርሱም አድሮ ለዓለም ያስተማረ እርሱ ነው፡፡ ‹‹ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ማሕየዊ ዘሠረፀ እም አብ ንስግድ ሎቱ ወንሰብሖ ምስለ አብ ወወልድ ዘነበበ በነቢያት…›› እንዲል ጸሎተ ሃይማኖት፡፡
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነትም መንፈስ ቅዱስ ያላደረበት አእምሮ ሊረዳው አይችልም፡፡ዓለም ይህንኑ(ነገረ ሥጋዌን) በተለያየ ፍልስፍናና አስተሳሰብ ለመተንተን እየሞከረ በስህተት ገደል የሚወድቅ ለዚህ ነው፡፡ስምዖን ጴጥሮስ በፊሊጶስ ቂሣርያ‹‹አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ›› ብሎ ሲመሰክር ጌታ መልሶ ሥጋዊ ደማዊ አእምሮ አልገለጠልህም የሰማዩ አባቴ እንጂ(አሐቲ ሥምረት መሆኑን ልብ ይሏል) በማለት የነገረው፤ባጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጦ የታየ ጌታችንን አምላክ ወልደ አምላክ ብሎ ማመን ለሥጋዊአእምሮ ጠጣር በመሆኑ ነው፡፡
ሐዋርያት ምሥጢረ መንግስትን እንዲያውቁ የሙሴና የነቢያት መጻሕፍትን ሁሉ እንዲያስተውሉና እንዲተረጉሙ በአጠቃላይ ሰማያዊ የሆነውን እውቀት ሁሉ የገለጠላቸው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ቅ.ጳውሎስ ‹‹…እንዲሁም ደግሞ ከእግዚአብሔር መንፈስ በቀር ለእግዚአብሔር ያለውን ማንም አያውቅም፡፡እኛ ግን ከእግዚአብሔር እንዲያው የተሰጠንን እናውቅ ዘንድ ከእግዘብሔር የሆነውን መንፈስ እንጂ የዓለምን መንፈስ አልተቀበልንም፡፡›› ብሏል ጨምሮም ‹‹ደግሞ የወንጌልን ምሥጢር በግልጥ እንዳስታወቅ አፌን በመክፈት ቃል ይሰጠኝ ዘንድ ስለ እኔ ለምኑ››በማለት ምስጢር ገላጭ የሆነ እርሱ ብቻ መሆኑን አሳውቋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ትንቢት መናገርም ሆነ ትንቢትን መተርጎም ከመንፈስ ቅዱስ መሆኑን ሲያስረዳ‹‹ይህን በመጀመሪያ እወቁ፤በመጽሐፍ ያለው ትንቢት ሁሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደም፤ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ፡፡ 2ጴጥ1÷20-21፤1ቆሮ2÷11-12፤ ኤፌ6÷19
ሰዎች በትዕቢት ሲያዙ ደግሞ የሚያነቡትን እንዳያስተውሉ ምሥጢርን ይሰውራል፡፡ ሐዋርያት ጌታችንን ለምን በምሳሌ እንደሚያስተምር ሲጠይቁት ‹‹ለእናንተ የመንግስተ ሰማያትን ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቷችኋል ለእነርሱ ግን አልተሰጣቸውም››ያለ ይህን ለማመልከት ነው፡፡ቅዱስ ጳውሎስም‹‹ወንጌላችን የተከደነ ቢሆን እንኳ የተከደነባቸው ለሚጠፉ ነው፡፡››ብሏል፡፡በቆሮንቶስ መልእክቱም ዓለም በጥበቧና በምርምሯ እግዚአብሔርን ለማወቅ እንዳልቻለች በተብራራ ሁኔታ ተገልጿል:: ማቴ13፥10-11፤ 1ቆሮ1÷18-27፤2ቆሮ4÷3 ስለዚህ ከትዕቢተኞች ምሥጢር የሚሰውር መንፈስ ቅዱስ ለትኁታን ደግሞ ስለሚገልጥ ከሣቲ ተብሏል፡፡
7. አለባዊ ማለት ማስተዋልን የሚሰጥ ማለት ነው፡፡ሰዎች ጌታ እግዚአብሔርን እንደ እግዚአብሔርነቱ መጠን ሳያከብሩት ሲቀሩና ኃጢአት መሥራት ሲደፋፈሩ ለማይረባ ከንቱ አእምሮ ተላልፈው ይሰጣሉ፡፡ከንቱ አእምሮ ማለት ማስተዋል የተሳነው ለመምረጥ ለመወሰን በሚሰራውም ነገር የሚጠብቀውን ውጤት(ፍርድ) ለመረዳት የተዘጋበት፤ ምክር የማይሰማና ተግሳጽ የማይቀበል ማለት ነው፡፡
ማስተዋል የተነሳቸው ለከንቱ አእምሮ ተላልፈው የተሰጡ ሰዎች የጌታ እግዚአብሔርን መኖር ይክዳሉ በግብራቸውም ከእንስሳት አንሰው ይታያሉ፡፡‹‹ልብ እንደሌላቸው እንስሳት ሆኑ››ያለው መጽሐፉ እንደነዚህ ያሉትን ነው፡፡በነቢዩ በኢሳይያስ‹‹ሂድ ይህን ሕዝብ መስማትን ትሰማላችሁ አታስተውሉምም ማየትንም ታያላችሁ አትመለከቱምም በላቸው›› በሚል ጠባያቸው ተገልጿል፡፡ ኢሳ 6፥9፤ሮሜ 1፥20-28
ጌታ መንፈስ ቅዱስ እውቀት በማጣት ጨለማ ላለ ሕዝብ እግዚአብሄርን የማወቅ ብርሃንን እንዲያይ ማስተዋልን ይሰጣል፡፡ዮሐንስ መጥምቅ ጌታችንን አያውቀው እንደነበርና ለእርሱም የገለጠለት መንፈስ ቅዱስ እንሆነ መስክሯል፡፡ዮሐ1÷3
ጌታችን ሐዋርያትን ብዙ ነገር ከነገራቸው በኋላ ከዚያም በላይ ሊነግራቸው ይችል እንደነበር እነርሱ ግን በነበሩበት ደረጃ ቢነግራቸው ለማስተዋል እንደማይችሉ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ግን እንደሚመራቸው (ማስተዋልን እንደሚሰጣቸው) እንዲህ ሲል ነግሯቸዋል፤‹‹የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም፡፡ ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል…ዩሐ16÷12-13 ቤተክርስቲያን በቸርነቱ እየጠበቀ በምግብናው የሚመራት ጌታ መንፈስ ቅዱስን‹‹ሀበነ እግዚኦ አዕይንተ አእምሮ ወትረ ኪያከ ይርአያ ወአዕዛንነሂ ቃለ ዘባህቲትከ ይስምዓ››ስትል በጸሎቷ ትማልላለች፡፡ዓይነ ሥጋችን ግዙፉን ዓይነ ልቡናችን ረቂቁን፤አንድም ዓይነ ሥጋችን ሥነ ፍጥረትህን በማየት ዓይነ ልቡናችን ቸርነትህን ምህረትህን መግቦትህን በማስተዋል አንተን ብቻ ማየት(ማምለክ) እንድችል፤ዕዝነ ሥጋችንና ዕዝነ ልቦናችንምሕይወት የሆነ ያንተን ቃል ብቻ መስማት ይችል ዘንድ አቤቱ ስጠን ስትል ነው፡፡
ካለ መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ጥበብን ይልቁንም መንፈሳዊ ጥበብን(ምሥጢርን) ገንዘብ አደርጋለሁ ማለት ከንቱ ነው፡፡የጠቢባንን ምክር የአዋቂዎችንም ማስተዋል የሚያስረሳቸው እርሱ በትኅትና በየዋህነት ደጅ ለሚጠኑ ሁሉ ግን ማስተዋልን ይሰጣል፤ፈቃዱ እንዱሁ ነውና፡፡