Login
Main menu

ጰራቅሊጦስ

Index

 

8. መስተናግር ማለት ሃይማኖትን፣ የጥበብን ቃል፣ ምሥጢርን የሚያናግር የሚያስተረጉም ማለት ነው፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ በበዓለ ሀምሳ በአይሁድ መካከል ቆሞ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ቢናገር በአንድ ጊዜ ስብከት ሦስት ሺ ሰዎች ማሳመን ችሏል፡፡ ይህ የሆነው ከቅዱስ ጴጥሮስ ዝግጅት ሳይሆን ‹‹ጉሽ የወይን ጠጅ ጠጥተዋል›› ብለው ሲያሙ ለነበሩ አይሁድ የተሰጠ የመንፈስ ቅዱስ መልስ ነበር፡፡ቅዱስ ጳውሎስ‹‹…ነገር ግን መንፈስ ቅዱስን መግለጥ ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል፡፡ለአንዱ ጥበብን መናገር በመንፈስ ይሰጠዋልና፤ለአንዱም በዚያው መንፈስ እውቀትን መናገር ይሰጠዋል…ለአንዱም ትንቢትን መናገር…ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር…ይሰጠዋል››ሲል የመንፈስ ቅዱስን የማናገር ኃይል አብራርቷል፡፡እንግዲህ በዋናነት መንፈስ ቅዱስን መስተናግር(የሚያናግር)ስንል፡-

ሀ. ሀብተ ትንቢትን ሰጥቶ ኃላፍያትን መጻእያትን የሚያናግር

ለ.የጠፋውን ለመመለስ የጠመመውን ለማቅናት የጥበብን ቃል የሚሰጥ(የሚያናግር)

ሐ.የሃይማኖትን ቃል ለማቅናት እውቀትን(ምሥጢር በመተርጎም) የሚናገር

መ.ለእያንዳንዱ ነገድና ሕዝብ ቋንቋውን ተናጋሪ ኅብረተሰብን መስሎና ተካክሎ መናገር ማለት ነው፡፡ 1ኛ ቆሮ 12፥4-11

ከዚህ የሚልቀው ደግሞ እነሆ፡-

‹‹ለእርሱና ለአሕዛብም ምስክር እንዲሆን ስለ እኔ ወደ ገዥዎች ወደ ነገሥታትም ትወስዳላችሁ፤አሳልፈውም ሲሰጡአችሁ የምትናገሩት በዚያች ሰዓት ይሰጣችኋልና እንዴት ወይስ ምን እንድትናገሩ አትጨነቁ በእናንተ የሚናገር የአባታችሁ መንፈስ ነው እንጂ የምትናገሩ እናንተ አይደላችሁም››ማቴ 10፥18-20

ጌታችን በሰማዕትነት ሰዓት ከነገሥታቱና ከጠቢባኑ በእኛ ያለውን እውነትና ተስፋ ለማስተሐቀር እንዲሁም በሀይማኖታችን ለመዘበት ለሚያነሱት ጥያቄና ክርክር እንዳንጨነቅ በዚያኑ ሰዓት በእኛ ውስጥ ያለ ጌታ መንፈስ ቅዱስ የምንናገረውንና ተከራካሪዎቻችንን የምናሳፍርበትን ቃል እንደሚሰጠን የተናገረው ማረጋገጫ ነው፡፡

9. መስተሥርዪ፡-መንፈስ ቅዱስ መስተሥርዪ ይባላል፡፡ኃጢአትን የሚያርቅ የሚያስወግድ የሚደመስስ ማለት ነው፡፡መንፈስ ቅዱ በአርባ በሰማንያ ከተጠመቅንበትና ከሥላሴ ልጅነትን ካገኘንበት ቀን ጀምሮ በእኛ ያድራል፡፡ሃይማኖትን ካልካድን በስተቀር አይለየንም፡፡ይህን ሲያይ ነው ቅዱስጳውሎስ ‹‹የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆናችሁ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንዲኖርባችሁ አታውቁምን?›› ያለው፡፡ 1ኛ ቆሮ 3፥16

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአታችንን ሊሽር በደላችንንም ሊደመስስ የመጣ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ አሐቲ ሥምረት ነው፡፡ኤፍሬም ሶርያዊ‹‹እስመ በፈቃዱ ወለሥምረተ አቡሁ ወመንፈስ ቅዱስ መጽአ ወአድኃነነ›› እንዳለ፡፡ ውዳሴ ማርያም ዘሠሉስ፡፡ በአባቱ በራሱና በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ መጥቶ አዳነን ማለት ነው፡፡ይህቺ ሥምረት(ፈቃድ) አንዱ ቀድሞ አስቦ ለሌላው የሚገልጻት መቀዳደም መለያየት ያለባት አይደለችም አንዲት ናት አንጂ፡፡ሰው በልቡ የሚያስበው ከመንፈሱና ከቃሉ መወቀዳደም እንደሌለበት ማለት ነው፡፡በመሆኑም በሰው ልጅ መዳን ውስጥ የፈቃድ መለያየት የለምና መንፈስ ቅዱስመስተስርዪ ይባላል፡፡አንድም

     በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸሙ ምሥጢራት ሁሉ የሚፈፀሙ(የሚከብሩ)በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡በጥምቀት ለሚገኝ ሥርየተ ኃጢአት ፈጸሚው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ኃጢአተኛ ንስሐ በሚገባ ወቅት በካህኑ ላይ አድሮ የሚናዝዝ የኃጢአትንም ሥርየት የሚሰጥ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ጌታችን ከትንሳኤው በኋላ ‹‹እፍ ብሎ መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፤ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል›› በማለት ለሐዋርያትሥልጣነ ክህነትን ሰጥቷቿል፡፡ በዚህ ዓለም የካህናት ተግባር ሰዎች ሁሉ ስለኃጢአታቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታንና ሥርየትን እንዲያገኙ ማገልገል ነው፡፡በጥምቀት፣በማስተማር፣በመምከርና በመገሰፅ፣በመናዘዝ፣እንዲሁም ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን በማቀበል በስሙ የሆነ የኃጢአት ሥርየትን መስበክ የምሥጢረ ክህነት ዋና ተግባር ነው፡፡በመሆኑም ክህነትን ከመስጠት ጀምሮ ምሥጢራት ሁሉ የሚፈጸሙ በመንፈስ ቅዱስ በመሆኑ መስተሥርዪ ተብሏል፡፡ ዮሐ 20፥22-23

     መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ ቅዱስ በሚመጣ ጊዜ ስለ ሶስት ነገር ዓለምን እንደሚወቅስ ተናግሯል፡፡ ‹‹…እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፡፡ ስለ ኃጢአት በእኔ ስለማያምኑ፤ ስለ ጽድቅም ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው፤ ስለ ፍርድም የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው›› ዮሐ16÷8-11

     በዘመነ ሐዲስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ተገልጦ ዓለምን ማዳኑን ከመካድ በላይ ኃጢአት የለም፡፡መንገድ ሕይወትና እውነት የተባለች በእርሱ ያለን ይህቺ ሃይማኖት ናት፡፡ሃይማኖትን መካድ ከመንፈስ ቅድስ ልጅነት የመለየት መጨረሻው ምልክት ነው፡፡

     በአንጻሩ ወረደ፣ተወለደ፣ተሰቀለ፣ሞተ፣ ተነሣ፣ ወደ ሰማይ ወደ አባቱ ዐረገ፣ ፣ዳግመኛም ለፍርድ ይመጣል ብሎ ከመመስከር የበለጠ ጽድቅም የለም፡፡ ቅ.ጳውሎስ‹‹እግዚአብሔርን የመምሰል ምሥጢር ያለ ጥርጥር ታላቅ ነው፤በሥጋ የተገለጠ፣ በመንፈስ የጸደቀ፣ለመላእክት የታየ፣በአሕዛብ የተሰበከ፣ በዓለም የታመነ፣በክብር ያረገ››1ጢሞ3÷16 ብሎ ክርስተናን በጥቅል ያስቀመጠ ለዚህ ነው፡፡ሐዋርያት በአጽናፈ ዓለም ጻድቃን በገዳም ሰማዕታት በደም የፈጸሙት ጽድቅም ይኸው ነው፡፡ ሁሉም አምላክ ሰው ሰውም አምላክ የመሆኑ ሕያው የሕይወት ምስክሮች ናቸው፡፡

     መንፈስ ቅዱስ የዚህ ዓለም ገዢ የተባለ ዲያቢሎስ እንደተፈረደበትም አብስሯል፡፡ፍርዱ ግን በዲያብሎስ ብቻ አይደለም በክህደት በኃጢአት እርሱን በሚመስሉት ላይ ሁሉ እንጂ፡፡ዮሐንስ በወንጌሉ‹‹በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና፡፡…በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤በማያምን ግን በአንድ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈረዶበታል››ዮሐ3÷16-19 ብሎ የዲያብሎስን የክህደት መንገድ የመረጡ ከጸጋ መንፈስ ቅዱስ ከመንግስተ እግዚአብሔር በአፍአ የሚጣሉ መሆናቸውን ገልጿል፡፡ ዲያብሎስን በግብር በክህደት የሚመስሉት ሁሉ ፍጻሜያቸው እርሱ በሚኖርበት መኖር በእርሱ ላይ የተፈረደውንም መቀበል ነው፡፡

     ጌታ መንፈስ ቅዱስ ይህን ሁሉ የሚሠራ እኛ ለዘላለም በሕይወት እንኖር ዘንድ ነው፡፡ ራሳችንን ለፈቃዱ ካስገዛን፤የእርሱ ማደሪያ መቅደሶች መሆናችንን አውቀን ህዋሳቶቻችንን ሁሉ በቅድስና ከጠበቅን በቅዱሳን ላይ አድሮ የሥራውን ሥራ በእኛም አድሮ ይሠራል፡፡ ሕይወትን ከሚሠጥ ከእርሱ ጋርም ለዘላለም በሕይወት እንኖራለን፡፡ሃይማኖትን ከመልካም ሥራ አስተባብረን እንድንይዝ በጌታችን በደሙ መገዛታችንንም ከንቱ እንዳናደርግ በማስተዋልም እንድንኖር ነው ቅዱስ ጳውሎስ‹‹ለቤዛም ቀን የታተማችሁበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ አታሳዝኑ››ያለን፡፡ኤፌ3÷30 የእግዚአብሔር ልጆች የመንግሥተ ሰማያት ዜጎች የመሆናችን ማረጋገጫ ማኅተማችን እርሱ ነውና፡፡

ዓለማትን የፈጠረ በነቢያት አድሮ የተናገረ በሐዋርያትም እውነትን ያስተማረ ጻድቃን ሰማእታትን ለገድል ያዘጋጀ እግዚአብሔርን መንፈስ ቅዱስ ሕይወታችንን ተረክቦ ይመራልን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁን! ጌታ ቢፈቅድ ብንኖር በሌላ የሕይወት ቃል እስክንገናኝ የአብ ቸርነት የወልድ ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ ሕብረት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን!

ግንቦት2007

 

ቀሲስ ታምራት ውቤ


Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ