“መንሹ በእጁ ነው፤ ...... "
Index
እግዚአብሔር ከሰማይ የሰው ልጆችን ተመለከተ፤ ሁሉ ዓመፁ በአንድነትም ረከሱ፤
በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ የለም፤ ጉሮሮአቸው የተከፈተ መቃብር ነው በምላሳቸው ሸነገሉ፤ ከከንፈራቸው በታች የእባብ መርዝ አለ፤
አፋቸው መርገምንና መራራን ተሞልቷል፤ ደምን ለማፍሰስ እግራቸው ፈጣን ነው፤ ጥፋትና ጉስቁልና በመንገዳቸው አለ፤ የሰላምን መንገድ አላወቁአትምና፤
እግዚአብሔርን መፍራት በዓይናቸው ፊት የለም፡፡
በኢትዮጵያም ዛሬ በዲሞክራሲና በሰብዓዊ መብት ሽፋን ለእውነት በቆሙ ላይ ብዙ ግፍ ይፈጸማል፡፡ አንድ ሀገር ሕግ ካለው ሕግን ማክበር ያለበት ሕዝቡ ብቻ አይደለም፡፡ እንደ እኛ ባሥልጣናት አረዳድ ግን የእነርሱ ግዴታ ሕግን ማስከበር እንጂ ሕግ ማክበር አይደለም፡፡ የመንግሥት ሹመኞች በየደረጃቸውና እንደየአቅማቸው ሕግን ሲጥሱ ጠያቂ የለባቸውም፡፡ ለመጠየቅ የግድ ከሥልጣናቸው መውረድ አለባቸው፡፡ ተጠያቂነትን ስለሚፈሩትና ውጤቱንም ስለሚያውቁ ሥልጣን ለእነርሱ ሕዝብ ማገልገያ ሳይሆን የደኅንነታቸው ዋስትና ነው፡፡ በሁሉ ላይ የሠለጠነው እውነተኛው ፈራጅ አውድማውን ሊያጠራ በፍርድ ሲገለጥ ግን ሕጋችሁም፣ ሥልጣናችሁም ሆነ የሽንገላ አንደበታችሁ መደበቂያ አይሆኗችሁም፡፡ ልዑሉ ምን ሊያደርግ እንደሚችል ፈርዖንንና ናቡከደነፆርን አልጠቅስም፡፡ ትናንት አጠገባችሁ የነበሩና ዛሬ የሌሉትን ማየት በቂ ነው፡፡ ማየት ከቻላችሁ!!! እያንዳንዱ ሸፍጥ ግፍ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ነገ በሌላው ይቅርና በራሳችሁ ልጆችና የልጅ ልጆች ሳይቀር የተናቃችሁ፣ የተጠላችሁና የምትረገሙ ትሆናላችሁ፡፡ ነገ መልስ መስጠት ለሕሊናዬ ነው የምሠራው ብላችሁ እንደ መመፃደቅ ቀላል አይሆንም፡፡ ኢትዮጵያን ያደቀቀው ሕዝቡን የደኅንነት ሥጋት ላይ የጣለውና እግዚአብሔርም የተፀየፈው ባልተገራ ኅሊናችሁ ላይ መደገፋችሁን ነው፡፡
በቤተ አይሁድ በመንግሥት አስተዳደር መዋቅር ላይ የተቀመጡትም ሠርቶ ለማደር ደፋ ቀና የሚለውን ለፍቶ አደር ከተፈቀደው በላይ ቀረጥ እየጫኑ ያስጨንቁት ነበር፡፡ በዚህም ነው ዮሐንስ ቀራጮችን “ከተፈቀደላችሁ አብልጣችሁ አትውሰዱ” ሲል የገሰፃቸው፡፡ በኢትዮጵያ እየተፈጸመ ያለው ግን ለመናገር የሚያስጨንቅ ነው፡፡ በመጽሐፍ “ሕዝቤን እንደ እንጀራ የሚበሉ አያውቁምን?” ተብሎ እንደ ተጻፈ በዚህ የከበሩ ሁሉ በቁም ሳሉ ጭንቀትና ደዌ ሲሞቱ ደግሞ የእግዚአብሔር ፍርድ የሚበላቸው ናቸው፡፡ ቢፈጥንም ወይ ቢዘገይም በችግር ከደረቀ ሰውነቱ የሚወጣ የደሃ ዕንባ መልስ ማግኘቱ አይቀርም፡፡
ሕዝብ ለመጠበቅ ቃል ኪዳን የፈጸሙ ወታደሮችም የደመወዛቸውን ማነስ ለማካካስ ሰውን መማለጃ ለመቀበል በሀሰት እየከሰሱ ያስጨንቁ ነበር፡፡ የታመነው ሰባኪ ጭፍሮች ሲጠይቁት “በማንም ላይ ግፍ አትሥሩ፤ ማንንም በሀሰት አትክሰሱ፤ ደመወዛችሁም ይብቃችሁ” በማለት ያለ ፍርሃት በደላቸውን ነግሯቸዋል፡፡ በሀገራችን የሕግ መከበር የሌለው ሕግ ስለ ሌለ ሳይሆን ሕግ አስፈጻሚ አካላት በተለያየ ምክንያት (ሙስና፣ ዘር፣ ሃይማኖት፣ ቡድን፣ የፖለቲካ አመለካከት፣ ወዘተ .
. .) ስለሚሸረሽሩት ነው፡፡ ብልሹ ሕግ አስፈጻሚዎች ባሉበት እንኳን የሰዎችን ቀርቶ ፍፁም ንፁህ የሆነውን ሕገ እግዚአብሔርን ማስፈጸም እጅግ ከባድ ነው፡፡
ከላይ የተጠቀሱትን ሁሉ መምከር፣ መገሠፅና ማስተካከል ያለበት የቤተ ክህነቱም በተመሳሳይ ነቅዞ ነበር፡፡ ሥርዓት ደንጋጊና ሕግ አስፈፃሚ የሆነ አካል ራሱ የእግዚአብሔርን ሕግ ከናቀ የጥፋት ሥር ይሆናል፡፡ ከውድቀት (ከጥፋት) በፊት በአይሁድ መካከል የታየ የመጀመሪያ ምልክት ከፍተኛ የሆነ መከፋፈል ነበር፡፡ ፈሪሳውያን፣ ሰዱቃውያን፣ ኤሴያዊያን፣ ቀነናውያን ወዘተ . . . ተብለው በቡድን ተከፋፍለዋል፡፡ አንዱ ከአንዱ ጋር አይተባበርም ነበር፡፡ ኢትዮጵያንና ቤተ ክርስቲያንንም ይኸው የመከፋፈል ምች የመለያየት ዋግ መቷቸዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ”አይሁዳዊ ግሪካዊ የለም ሴት ወንድ ጌታ ሎሌ የለም ሁሉ በክርስቶስ አንድ ሆኗል” የሚለው ተረስቶ በዘር መሳሳብ ሰልጥኖብና፡፡ መከፋፈል መለያየት ደግሞ የውድቀት ዋዜማ መሆኑ የታመነ ነው፡፡