“መንሹ በእጁ ነው፤ ...... "
Index
ሁለተኛው ምልክት ቤተ መቅደሱን የንግድ ማዕከል ማድረጋቸው ነበር፡፡ የቤተመቅደሱ አገልጋዮችም የእስራኤልን አምላክ አንደ አባቶቻቸው በፍቅርና በቅንዓት ከማገልገል ይልቅ በጥቅም ታውረው፤ ቤተ መቅደሱንም በሀብት መክበሪያ አድርገውት ነበር፡፡ ይህ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን እያታየ ያለ ምልክት ነው፡፡ አገልጋዮች ምንደኞችና ላልተገባ ጥቅም ተላልፈን የተሰጠን ሆነናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በገቢ ራሷን መቻሏን የሚጠላ ማንም ባይኖርም በፋይናንስ ከመጠንከር በላይ ግን በእምነት፣ በጸሎት፣ በመንፈስ፣ በእውነት፣ በሕይወት፣ በተጋድሎ ወዘተ … መጠንከር ይጠበቅበታል፡፡ ዓለምን፣ የጨለማ አበጋዞችንና መልዕክተኞቻቸውን ድል እየነሳች እዚህ የደረሰች በእርሱ ነውና፡፡ ባሏት ይዞታዎች ላይም መገንባት ያለባት ለሰው አካላዊ፣ አእምሯዊና መንፈሳዊ እድገት የሚጠቅም ተቋም እንጂ ሀብት ለማከማቸት ብቻ መሆን የለበትም፡፡ የቤተ መቅደሱ ባለቤት አይሁድን “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፣ እናንተ የሌቦችና የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት” ቢላቸውም በምህረት የተገለጠ ተግሳፁን ናቁ፡፡ እኛም የአይሁድ ወራሾች ሆነን መቅደሱን አቃለናል ተግሣፁንም ንቀናል፡፡
ሶስተኛው ምልክት የመኳንንትን ሥልጣን በመፍራት እውነትን አለመግለጥ ነበር፡፡ ሄሮድስ የወንድሙን ሚስት እስከ ማግባት ኃጢአት ሲሠራ ባህታዊው ዮሐንስ እንጂ ቤተ ክህነቱ ትንፍሽ አላለም፡፡ በዘመኑ የነበረው የአይሁድ ቤተ ክህነት ዘማውያን ባለሥልጣናትን የሚታገሥ ለድሆች የሚራራ ድውያንን የሚፈውስ ንጹሑን ጌታ ግን የሚከስ ነበር፡፡ ለምድራዊ ገዥዎች እጅ የሰጠች ቤተ ክህነት ተቀንዮቷ ለምድራዊ ጌታ ስለሆነ ሰማያዊውን አደራ ለመፈጸም አቅም አይኖራትም፡ ቤተ ክርስቲያን በዓለም ተገልጣ ታየች እንጂ ከዓለም አይደለችም፡፡ እግዚአብሔርን ከሚፈሩ እንጂ ነገ ወደ አፈርነት ከሚቀየሩ ዕቡይ ምድራዊ ገዦች ጋር ኅብረትም የላትም፡፡ እየሆነ ያለው ግን በተቃራኒው ነው፡፡
አራተኛው ምልክት የእግዚአብሔር ባላደራዎች የነበሩት ካህናትና የሕግ መምህራን ሕዝቡን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ በእውነትና በቁርጠኝነት ከመሥራት ይልቅ የልብሳቸውን ዘርፍ በማስረዘምና አሸንክታብ በማብዛት መንፈሳዊ ለመምሰል መሞከራቸው ነው፡፡ የነበሩበትን ግብዝነት ጌታችን ገልፆ ነግሯቸው ነበር፤ ግን አልተመለሱም (ማቴ 23 ተመልከት)፡፡ ካህናተ ሀዲስን ከፈሪሳዊያን እርሾ ተጠበቁ አለን፡፡ ነገር ግን በተቃራኒው በተከለከልነው እርሾ ቦክተን ማዕዳችንን የኮመጠጠ ሞላነው፡፡
አምስተኛው ምልክት በቤተ ክህነቱና በመናንያኑ መካከል የነበረው መቃቃር ነው፡፡ ኤሴያውያን በሚል መጠሪያ የሚታወቁት መናንያን በቤተ መቅደስ የሚፈፀመውን ነውር ከመጠየፋቸው የተነሳ ግንኙነታቸውን ጨርሰው አቋርጠው በዮርዳኖስ በረሃ ተከተው ይኖሩ ነበር፡፡ ጌታችን በበረሃ የጾመው በቤተ መቅደስም ያስተማረው ሁለቱንም አገልግሎት ባርኮ ሊሰጥ ነው፡፡ በዘመናት ቤተ ክርስቲያን የተጠበቀችውም በመናንያን ጸሎትና በመምህራን ትጋት ነው፡፡ ዛሬ ግን ገዳማውያኑ ቤተ ክህነቱን እንደ ዓለማዊ ቆጥረው ቤተ ክህነቱም መናንያኑን ማማከርን ችላ ብሎት የተናጠል ጉዞውን ተያይዘነዋል፡፡ ሁለቱን አስተሳሰሯቸው ያለ መዋቅር እንጂ መንፈስ እንዳልሆነ በግልፅ እየታየ ነው፡፡
ስድስተኛው ምልክት ሢመት ነው፡፡ በሕገ ኦሪት መሰረት የሚሾም አንድ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ቤተ አይሁድ ግን ቤተ መቅደሱ ላይ ሥርዓት ጥሰው ሕግ አፍርሰው አንዱ ሊቀ ካህናት ሳይሞት ሌላ ሾመው ሀናና ቀያፋ በተባሉ በሁለት ሊቃነ ካህናት ይመሩ ነበር፡፡ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንም አንዲት ቤተ ክርስቲያን ሊኖራት የሚገባ ፓትርያርክ አንድ ብቻ ነው፡፡ አሁንም ግን የሆነውና እየሆነ ያለው ግን በተቃራኒው ነው፡፡
በዚህ ጊዜ ነው አውድማን ሊያጠራ መንሽ የያዘው የተገለጠው፡፡
ዮሐንስ መጥምቅ በአውድማው ላይ ሥልጣን ያለውን መምጣት የገለፀው እንዲህ ሲል ነው፡፡ “እናንተ የእፉኝት ልጆች ከሚመጣው ቁጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ? እንግዲህ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤ በልባችሁም አብርሃም አባት አለን እንደምትሉ አይምሰላችሁ፡፡ እላችኋለሁና ከእነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሳለት ለእግዚአብሔር ይቻለዋል፡፡ አሁንም ምሳር በዛፎች ሥር ተቃጥቷል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል፡፡ . . . መንሹም በእጁ ነው፤ አውድማውንም ፈጽሞ ያጠራል፤ ስንዴውንም በጎተራው ይከታል፤ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል፡፡”
አንባቢው ያስተውል! በአይሁድ ሕዝብ፣ ገዥዎችና ቤተ ክህነት ዘንድ ይፈፀም የነበረው ጌታ እግዚአብሔርን የሚሳዝን በደል በልዑሉ ቁጣ ለመጠረግ ዋዜማ ነበር፡፡ እኒህ ሁሉ በእኛ መካካል መፈፀማቸውን ያስተዋለ ጥፋት በደጃችን እንደ ቀረበ ይወቅ፡፡ የእግዚአብሔር አውድማ ኢትዮጵያ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን በጊዜ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ ካልተገኘብን በአይሁድ የደረሰ እንደሚደርስብን የማያጠራጥር ነው፡፡ አውድማው ይጠራ ዘንድ ግድ ነው፡፡ እኛ እንዲህ ነን! የነእንትና ዘር ነን! አንፈርስም . . . አንጠፋም በሚል ፉከራ እርስ በርስ በመደላለል የምንኖርበት ሰዓት አብቅቷል፡፡ አሁን ባለ መንሹ ቆሟል፤
ምሳርም በዛፍ ሥር ተቃጥቷል፤ መቆረጥ ያለበት ሁሉ ይቆረጣል፡፡ ልዑሉን በመፍራት የሚኖሩ ግን ከፀጉራቸው አንዲት አትወድቅም፡፡ ለእነርሱ ሞትም ሆነ ሕይወት ለክብር ይሆናል!
ስልክ ይጠራል
ቀሲስ፡- ጤና ይስጥልኝ… እንዴት ከረሙ?
መልስ፡- እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን! በደህና ሰነበቱ ወይ ቀሲስ? ቀሲስ፡- ክብር ይግባው! ደህና ነኝ!
(መሀሉ አይነገርም)
ስንብት
ቀሲስ፡- እንግዲህ ጌታ እግዚአብሔር ምህረቱን እንዲያቀርብ መዓቱን እንዲያርቅ ጸልዩልን? መልስ፡- ዘመነ ዮሐንስን በደኅና ካለፍን ምንም አንሆን አይዟችሁ!
ቀሲስ፡- ዘመነ ሉቃስ ማለትዎ ነው?
መልስ፡- ኧኸ . . . ሉቃስማ አለፈ ዮሐንስን ነው እንጂ!
ቀሲስ፡- ኧረ እባካችሁ እኛ እኮ በጭንቅ አለቅን፡፡ እናንተ ሚስት ልጅ ውላጅ የለ ምንም አያሳስባችሁ፡፡ እኛ ግን እዚህ በጭንቀት አለቅን፡፡
መልስ፡- አዬ እሱን እንኳ ተውት የሚጨነቅ ማን እንደሆነ ባለቤቱ ያውቃል፡፡ ለማንኛውም ዘመነ ላህም አልፎ የሚተካው ዘመነ ንስር ስለሆነ እንደ ንስርነቱ የሚለቀመውን ለቅሞ ሰላም ይሆናል አይዟችሁ!
ቀሲስ፡- እንግዲያው ከሚለቀሙት እንዳንሆን በጸሎታችሁ አስቡን?
መልስ፡- ደግ ዛዲያ ምን ይዘን ኖሯል? አይዟችሁ! ጸሎተ አበው ይጠብቃችሁ! ቀሲስ፡- አሜን!!!
“ለእኔም ዘመኑ ቀርቧልና የዚህን መጽሐፍ . . . ቃል በማኅተም አትዝጋው፡፡ ዓመፀኛው ወደ ፊት ያምፅ፤ ርኵሱም ወደ ፊት ይርከስ፤ ጻድቁም ወደ ፊት ጽድቅን ያድርግ፤ ቅዱሱም ወደ ፊት ይቀደስ”
በአዲስ ዓመት መልካም አዲስ ሕይወት!
ተጻፈ ኅሊናቸው ላልተቀሰፈ በጳጉሜን 2011 ዓ.ም ቀሲስ ታምራት ውቤ