Login
Main menu

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል ሰባት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

መግቢያ፡ በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

ሌላው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የባህርይ አምላክነቱን ከገለፀባቸው ባህርያት አንዱ ኃጢአትን የማስተሰረይ(ይቅር የማለት) ሥልጣኑ ነው፡፡

በመጽሐፍ እንደተፃፈ ኃጢአትን ማስተሰረይ ብቸኛ የቅዱስ እግዚአብሔር ሥልጣን ነው፡፡ በማር.ወን 25- ላይ ሽባውን ሰው እንዲፈውስላቸው በአልጋ አድርገውና የቤቱን ክዳን ነቅለው በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ፊት ሲያቀርቡት አንተ ሰው ኃጢአትህ ተሰረየችልህ ነበር ያለው፡፡ በዚያ የነበሩ አይሁድም "ይህ ሰው በርግጥ ይሳደባል ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር ኃጢአትን ያስተሰርይ ዘንድ ማን ይችላል?" በማለት ሲያጉረመርሙ ጌታችን ግን "የሰው ልጅ ኃጢአትን ያስተሰርይ ዘንድ ሥልጣን እንዳለው እንዲያውቁ አስረግጦ ነግሯቸዋል፡፡ ሽባውንም ፈውሶታል፡፡ እዚህ ላይ"የሰው ልጅ" እያለ ጌታ የሚጠራው ራሱን እንደሆነ አስተውል፡፡

ኃጢአት የሚሠራ ሰው በዋናነት የሚበድለው ቅዱስ እግዚአብሔርን ነው፡፡ ምክንያቱም፡

1. ሕጉን ይተላለፋል አድርግ የተባለውን ሲያስቀር አታድርግ የተባለውንም ሲያደርግ የአግዚአብሔርን ሕግ ማቃለሉ አይደለምን?፡፡ ለልዑል እግዚአብሔር ፍቅርና ክብር እንዳለን የሚታወቅበት ብቸኛ መንገድ በቃሉ(በሕጉ) ታዛዥ ሆነን መገኘት ነው፡፡ ይህ ካልሆነ ዓመፀኞች ነን፤ ዓመፃ ደግሞ ኃጢአት ነው፡፡ ኃጢአትንም የሚያደርግ ከእግዚአብሔር አልተወለደም፤እግዚአብሔርንም አያውቀውም፡፡ 1ዮሐ 2

2. እግዚአብሔርን የሚበድለው የፈጠረውን ፍጥረት በማሳዘኑ ነው፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር የፍጡራኑ በደልና ሥቃይ የሚሰማው አምላክ ነው፡፡ ገዢያችን አባታችን ነውና፡፡ የግዛቱ መደፈርና የህዝቡ በጦርም ሆነ በምርኮ መንገላታት ንጉስን ከዙፋኑ አውርዶ ከቤተመንግስቱ አስወጥቶ ጦርነት እንደሚያስከትተው፤የሚስቱ የልጆቹ መጠቃት የአባትን ቁጣ ቀስቅሶ ለበቀል አንደሚያነሣሣው ለልዑል እግዚአብሔርም የፍጡራኑ መበደል አንዲሁ ነው፡፡ ከዚያም በላይ ከአካላችን አንዱ ብልት ላይ የሚደርስ አደጋ ህማሙ ነፍሳችን እንደሚሠማት ለጌታ እግዚአብሔርም በፍጡራኑ ላይ የሚደርስ ጥቃት እንዲሁ ነው፡፡

በመሆኑም ሰው ኃጢአት ሠርቶ ባልንጀራውን ቢበድል ይቅርታን ማግኘት ያለበት ከተበዳዩ ብቻ ሳይሆን በዋናነት ከልዑል እግዚአብሔር ነው፡፡ ምሳሌ፡- አንድ ሰው ለአቅመ ሔዋን ያልደረሰች ብላቴናን በግዳጅ ቢደርስባት ጥቃቱ(በደሉ) የእርሷ ብቻ ሳይሆን የቤተሰብ፣ የማኅበረሰቡና የመንግስት ጭምር ነው፡፡ ምንም እንኳ በዳዩ ሽማግሌ ልኮ ካሣ ከፍሎ ከተበዳይዋም ሆነ ከቤተሰቧ ይቅርታን ቢያገኝ የሀገሪቱን ሕግ በመተላለፉና በአንዲት ንፁህ ዜጋ ላይ ወንጀል በመፈፀሙ በመንግስት ሕግ ከመጠየቅ አይድንም፡፡ ማኅበረሰቡም ይህ ሰው ነገ ሊያደርሰው የሚችለው ተመሳሳይ በደል ሊታረም የሚችልበትን መንገድ ከመጠየቅ ችላ አይልም፡፡ ስለዚህ ያ ሰው ፍፁም ይቅርታን አግኝቻለሁ ብሎ በሰላም መኖር የሚችለው ከግል ተበዳይዋ፣ ከቤተሰቧ፣ ከማኅበረሰቡና ከመንግስት ይቅርታ ሲደረግለት ነው፡፡ በመንፈሳዊው ዓለምም ይኸው ነው፡፡ ሰው የግል ተበዳይን ብቻ ሳይሆን ቅዱስ እግዚአብሔርን ፍፁም ይቅርታ በሚጠይቅ ሰዓት ስርየትን ያገኛል፡፡ የአባቱን ሀብት ያባከነው ወጣት ወደቤቱ ሲመለስ ለአባቱ "በሰማይና በምድር ፊት በድያለሁ" ያለው ለዚህ ነው፡፡ በምድር ወላጅ አባቱን በሰማይ ያለ ፈጣሪውን በድሏልና፡፡ሉቃ 15

ስለዚህ በዚህ አግባብ ፍፁም የኃጢአት ይቅርታን ሊሠጥ የሚችል ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡ ዳዊት " ነፍሴ ሆይ እግዚአብሔርን አመስግኚ አጥንቶቼ ሁሉ የተቀደሰ ስሙን ነፍሴ ሆይ እግዚአብሔርን አመስግኚ፤ኃጢአትሽን ሁሉ ይቅር የሚል ከደዌሽ ሁሉ የሚፈውስሽ…"

በማለት የይቅር ባይነት ሥልጣን የቅዱስ እግዚአብሔር መሆኑን ይገልፃል፡፡ ጨምሮም…ኃጢአቴን ለአንተ አስታወቅሁ በደሌንም አልሸፈንሁም፤ ለእግዚአብሔር መተላለፌን እነግራለሁ አልሁ፤አንተም የልቤን ኃጢአት ተውህልኝ" እንዲሁም "አቤቱ ኃጢአትንስ ብትጠባበቅ አቤቱ ማን ይቆማል? ይቅርታ ከአንተ ዘንድ ነውና" በማለት ያስረግጣል፡፡መዝ 311-5፣ መዝ1021-14፣መዝ 129(130)3

ኃጢአትን ይቅር የማለት ሥልጣን የጌታ እግዚአብሔር መሆኑ ከታወቀ ኢየሱስ ክርስቶስ "ኃጢአትህ() ተሰረየችልህ()" ማለቱ እርሱ አምላክ(እግዚአብሔር) ለመሆኑ ጉልህ ማስረጃ ነው፡፡

ሉቃ748- ሽቱ የቀባችውን ሴት በቃሉ "ኃጢአትሽ ተሰረዮልሻል በሰላም ሂጂ" ብሎ ሲያሰናብታት በዚያ የነበሩ "ኃጢአትን ስንኳ የሚያስተሠርይ ይህ ማነው? እስከማለት ተገርመዋል፡፡

ሉቃ2343- በመስቀል ላይ ሳለ በቀኙ የተሰቀለ ወንበዴ በሰማይና በምደር የተፈፀሙ ተዓምራቶችን አይቶ "በመንግስትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ" ብሎ ላቀረበው የይቅርታ ልመና" ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ" በማለት የይቅርታ ባለቤት መሆኑን አሳይቷል፡፡

ሉቃ2446-"ክርስቶስ መከራ ይቀበላል በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ይነሣል፤በስሙም ንስሐና የኃጢአት ሥርየት ከኢየሩሳሌም ጀምሮ በአህዛብ ሁሉ ይሰበካል"፡፡ ልናስተውል የሚገባን በመጽሐፍ ቅዱስም ሆነ በዓለም ሃይማኖቶች ታሪክ ንስሐና የኃጢአት ሥርየት በስሙ የሆነ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ በቡድሐም፣ ሆነ በክሪሽና በዘራስተርም ሆነ በመሐመድ የለም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም በቀደምት አበው ሆነ በነቢያት፣ በነገስታት ከጌታም በኋላ በተነሱ በሐዋርያት፣ ጻድቃን ሰማዕታት ስም የኃጢአት ሥርየት አልተሰበከም፡፡ ሁሉ በእርሱ ከኃጢአት ነፁ ለዚሁም ምስክር ሆኑ እንጂ፡፡

የሐዋ.ሥራ 237-38- ቅዱስ ጴጥሮስ በበዓለ ጰራቅሊጦስ የሰበከውን የሰሙ ልባቸው የተነካ ሰዎች ምን እናድርግ ? ብለው በጠየቁ ሰዓት የተሰጣቸው መልስ "ንስሐ ግቡ ኃጢአታችሁ ይሠረይ ዘንድ በጌታ በእየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ" የሚል ነው፡፡

1ዮሐ11-10- ያየነውን እንመሠክራለን ያለ ዩሐንስ ወንጌላዊ "ኃጢአት የለብንም ብንል ውሸተኞች ነን … የልጁ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል…በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነፃን የታመነ ጻድቅ ነው፡፡" በማለት የኃጢአትን ይቅርታ እንዴት እንደሆነ ጽፎልናል፡፡

ኃጢአትን ይቅር የሚል በደልን የሚደመስስ ለሚወዱትም መንግሥቱን የሚያወርስ ጌትነቱ በሁሉ ላይ የሆነ በመጨረሻው ዘመን ግን የባርያን መልክ ይዞ የተገለጠ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ነው፡፡ ስለ ኀጢአታችን ብዙ ልንፆም፣ በፀፀት ልናለቅስ፣ በርካታ ምፅዋት ልንሠጥና በድካም እስክንዝል ልንሰግድ እንችላለን ፡፡ ይህ ሁሉ ግን ይቅርታውን ደጅ የምንጠናበት መንገድ እንጂ በራሱ ፍፁም ሆኖ ይቅርታን የሚያስገኝ አይደለም፡፡ ይቅርታን ለማግኘት ለኃጢአታችን መስዋዕት ሆኖ የቀረበ የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውን ልንበላ ክቡር ደሙንም ልንጠጣ የግድ ያስፈልገናል፡፡

መጽሐፍ "ያለ ደም ሥርየት የለም" እንዲል ጌታም በቃሉ "ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ህይወት አለው፡፡ ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛ መጠጥ ነውና፡፡ እውነት እውነት እላችኋለሁ ሥጋዬን ካልበላችሁ ደሜንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም"፡፡ እንዲል ዕብ፣ዮሐ 653

ጸሎት- ቅዱስ አምላክ ሆይ አናመስግንሀለን፡፡ ከቸርነትህ ገናናነት የተነሣ ሥጋህንና ክቡር ደምህን ለህይወት ለመድኃኒት እንዲሆነኝ ሰጥተኸኛል፡፡ ይህም በሕይወት ዘመኔ የተቀበልኩት በዋጋ የማይተመን እኔን የመውደደህ ስጦታ ነው፡፡ ቸር ሰውን ወዳጅ ሆይ ወደ ሕይወት መድኃኒት እንዳልቀርብ ዲያብሎስ በብዙ የምክኒያት ሰንሰለቶች አስሮኛልና ፍታኝ፡፡ ምክንያትን ቆርጬ የምጥልበትን ኃይል አድለኝ፡፡ በእኔም ዘንድ መኖርያህን ታደርግ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን!አሜን!

አቡነ ዘበሰማያት



ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

 



Read more...

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል አምስት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን የሚያውቅ የባህርይ አምላክ ስለመሆኑ፤

መግቢያ፡- ባለፉት ሳምንታት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ "ሁሉን ቻይ" አምላክ መሆኑን በተረዳ ነገር አይተናል፡፡ በዛሬው ጹሑፋችን አምላካዊ ባህርያት ከሆኑት አንዱን "ሁሉን ማወቅ" ከመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ በማስደገፍ እናያለን፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ምስጢሩን ይግለጽልን!

ሁሉን ማወቅ የእግዚአብሔር የብቻው /የተለየ/ ባህርዩ ነው፡፡ በሰማይም ሆነ በምድር ወይም በውቅያኖስ፣በብርሃንም ሆነ በጨለማ ፣ በቁሳዊውም ሆነ በመንፈሳዊው ዓለም እርሱ የማያውቀው ከእርሱ ተሰውሮ የሚፈጸም አንዳች ስንኳ የለም፡፡ ሁሉንም ከመሆኑ በፊት እንደተደረገ አድርጎ ያውቀዋል፡፡ በጸሎተ ኪዳን እንተፃፈ " እምቅድመ ህሊና ኲሎ የአምር፣ ወእምቅድመ ህሊና ይፈትን" ከህሊና አስቀድሞ ያውቃል፣ ከሀሳብም ቀድሞ ይመረምራል፡፡ ዓለምን ጅማሬው ላይ ሆኖ ፍፃሜውን ያውቀዋል፡፡ በአጭር ቃል ከእርሱ ምንም ምን አይሠወርም የክፍዎችንም ሆነ የበጎዎችን ምክር ያውቃል፣ የጠቢባንንም አሳባቸውን ይመረምራል፡፡ ከመሆኑ አስቀድሞ እንጂ ከተደረገ በኋላ ተመራምሮ በነገሩ የሚደርስ አይደለም፡፡ በመሆኑም አኛንም ማንም ከሚያውቀን ይልቅ ከራሳችንም በላይ ያውቀናል በመጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ተብሏል፡፡

1ሳሙ 2፥3 " አትታበዩ በኩራትም አትናገሩ፡ እግዚአብሔር አዋቂ ነውና…"

1ኛ ዮሐ 3፥20 " እግዚአብሔር ከልባችን ይልቅ ታላቅ ነውና ሁሉንም ያውቃል"

ይህ እንዲህ ከሆነ "ሁሉን አዋቂነት" የሚለው ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀፀል ይችላል ወይ? የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ምላሽ "በትክክል" የሚል ነው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ እነሆ፡፡

ማቴ9፥1-8 ጌታ እየሱስ ክርስቶስ በአልጋ የተኛ ሽባ ወደ እርሱ ባመጡ ጊዜ ሽባውን"አንተ ልጅ ኃጢአትህ ተሰረየችልህ" አለው፡፡ ከጻፎች ግን አንዳንዶቹ በልባቸው ይህስ ይሳደባል አሉ፡፡ ኢየሱስም አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አለ ስለምን በልባችሁ ክፉ ታስባላችሁ?...

ማቴ 12፥15 ጌታችን በሰንበት ስለፈወሰ ፈሪሳውያን ሊገድሉት ሲማከሩ ምክራቸውን አውቆ ከዚያ ፈቀቅ አለ ይላል፡፡

ማቴ 12፥22-27 ሕዝቡ በአጋንንት ላይ ባለው ሥልጣን ሲደነቁ ፈሪሳውያን ግን በአጋንንት አለቃ በብዔል ዜቡል አጋንንትን ያወጣል በማለት ሲያስቡ ኢየሱስ ግን አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው እርስ በርሷ የምትለያይ መንግስት አትፀናም…

ማቴ 17፥24-27 ቀረጥ ሰብሳቢዎች ጰጥሮስን በውጭ አግኝተው መምህራችሁ ግብር አይገብርምን? ብለው ሰለጠየቁት ጴጥሮስ ይህን ሊናገር ወደ ቤት ሲገባ አስቀድሞ የሆነውን አውቆ ዓሣ አጥምዶ ያገኘውን እንዲከፍል ነግሮታል፡፡

ሉቃ 5፥1-11 ቅዱስ ጴጥሮስ ሌሊቱን ደክሞ ያልሆነለትን በጌታችን ትዕዛዝ ብዙ ዓሣ በመያዙ ቢደሰትም በታላቅ ፍርሃት ጌታን "እኔ ኃጥአተኛ ሰው ነኝና ከእኔ ተለይ" ብሎታል፡፡ መተርጉማን ይህን የቅዱስ ጴጥሮስን ቃል ሲፈቱት የባህሩን ውስጥ እንዲህ ያወቀው የእኔንማ ልብ እንዴት ይመረምረው ብሎ እንደፈራ ያትታሉ፡፡

ሉቃ 7፥36-50 መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በስምዖን ፈሪሳዊ ቤት ለምሳ በተቀመጠበት ወቅት ባለ ሽቶዋ ማርያም እግሩን እየሳመች በእንባዋ እያጠበችና በፀጉርዋ እያበሰች ሽቶ ቀብታ ሰለኃጢአቷ ሥርየት በአርምሞ ስትማፀ ስምዖን ፈሪሳዊ አይቶ ይህስ ነብይ ቢሆን ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን እንደሆነች እንዴትስ እንደነበረች ባወቀ ነበር ኃጥአተኛ ናትና ብሎ በልቡ አሰበ፡፡ለዚህ ሰው የልቡን አውቆ  ምን ዓይነት አስደናቂ መልስ እንደሰጠው ቃሉን አንብብ፡፡

ሉቃ 8፥43-48 12 ዓመት ደም ይፈሳት የነበረች ሴት የነበረች ሴት ጌታን ህዝቡ እያገፋው ሳለ ተሰውራ የቀሚሱን ዘርፍ በመንካቷ ተፈወሰች ጌታም ማን ነው የነካኝ ብሎ ሲጠይቅ ሐዋርያት ህዝቡ ይገፉሃል ማነው የነካኝ ትላለህን? ሲሉት አንድ ሰው ዳሶኛል ኃይል ከእኔ እንደወጣ እኔ አውቃለሁና ብሎ ነው የመለሰው ሴቲቱም እንዳልተሠወረች ባየች ጊዜ እየተንቀጠቀጠች መጥታ በፊቱ ተደፋች የተደረገላትንም በህዝቡ ሁሉ ፊት መሠከረች፡፡

ሉቃ 22፥31-34 ጌታችን እንደሚያዝና ሁሉም ጥለውት እንደሚሸሹ በተናገረበት ምሴተ ሐሙስ ቅዱስ ጴጥሮስ ሌሎች ቢክዱህ እኔ አልክድህም ብሎ ለሠጠው የትምክህት መልስ" ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ እንደሚክደው ቀድሞ ነግሮታል፣ ይኸውም እንደቃሉ ተፈፅሟል፡፡

ዮሐ2፥5 " ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር፤ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር፡፡ ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና፡፡

ዮሐ 1፥47-50 ፊልጶስ ናትናኤልን ጋብዞ ወደ ጌታችን ባመጣው ሰዓት ጌታ "በልቡ ተንኮል የሌለበት የእስራኤል ስው እነሆ" በማለቱ ናትናኤል ከወዴት ታውቀኛለህ? ቢለው ፊልጶስ ሳይጠራህ ከበለስ በታች አየሁህ የሚል መልስ ሲሰጠው" መምህር ሆይ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፤አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ" በማለት እርሱ ሁሉን አዋቂ አምላክ ወልደ አምላክ መሆኑን መስክሯል፡፡

ዮሐ4፥1-መጨረሻ  በተፃፈው ፍፁም የሚመስጥ ታሪክ ሳምራዊቷ ሴት ለሀገሯ ሰዎች ከጌታችን ጋር ስለነበራት ቆይታ ስትገልፅላቸው ወደ እርሱ እንዲመጡም ስትጋብዛቸው "ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ…" ብላለች ቁጥር 29

ዮሐ6፥15 እንጀራ በልተው ሲጠግቡ እርስ በርሳቸው ከሆነስ አይቀር ስንራብ እያበላ ፣ስንጠማ እያጠጣ፣ስንታመም እየፈወሰ፣ስንሞት እያሰናዳ ቢገዛን መልካም በሆነ ኑ እናንግሠው ብለው ያሰቡትን አውቆ ከአጠገባቸው ፈቀቅ ብሎ ወደ ተራታ ወጣ ይላል፡፡

ዮሐ11፥1-መጨረሻ ፡- በቦታው በአካል ባይገኝም ስለአልዓዛር መታመምና መሞት ቀድሞ ለሐዋርያት ነግሯቸዋል፡፡

v  ጌታችን ስለሞቱና ትንሣኤው አስቀድሞ ተናግሯል፡፡

ማቴ 24፥1-መጨረሻ፡- የዓለም መጨረሻና የዳግም ምፅዓቱ ምልክቶችን አስቀድሞ ተናግሯል፡፡        ዮሐ16፥29-30 ሐዋርያት"እነሆ አሁን በግልጥ ትናገራለህ፣በምሳሌም ምንም አትናገርም ሁሉን እንድታውቅ ማንምም ሊጠይቅህ እንዳትፈልግ አሁን እናውቃለን፡፡

ዮሐ21፥15-17 በጥብርያዶስ ባህር ዳርቻ ጌታችን ከስምዖን ጴጥሮስ ጋር በነበረው ቆይታ "ትወደኛለህን?" ብሎ ሦስት ጊዜ ለጠየቀው ጥያቄ የሰጠው የመጨረሻ ምላሽ "ጌታ ሆይ አንተ ሁሉን ታውቃለህ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ " የሚል ነው፡ በዚህም ሁሉን አዋቂ መሆኑን አስረግጦ መስክሯል፡፡ በመቀጠል ጌታችንም ቅዱስ ጴጥሮስ በኔሮን ቄሣር ዘመን በምን ዓይነት ሞት እግዚአብሔር ያከብር ዘንድ እንዳለው ነግሮታል ይህም ሁሉን አወቂ መሆኑን ያስረገጠበት መንገድ ነው፡፡

ራስን መመዘኛ /መመርመርያ/ ጥያቄ!

 

.የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አዋቂነቱ በእኔ ሕይወት ውስጥ ያለው ተፅዕኖ ምን ያህል ነው?

ለ. በእርግጥ እግዚአብሔር ሁሉን አዋቂ መሆኑን በእውነት አምናለሁ?

. እግዚአብሔር ከሁሉን አዋቂነቱ ወሰን ተሠውሬ ኃጢአት ሠርቼ አውቃለሁን?

መ. ቅዱስ እግዚአብሔር / ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ / ከልቤ ጋር ያለው ግንኙነት ምን ያህል ነው? እንዴትስ እረዳዋለሁ?

 

v  በሀገር ውስጥ ላላችሁ ለጥያቄዎቹ መልስና ሀሳባችሁን በሪፖርት(በወረቀት) በጉባኤ ቀን ትሰጣላችሁ፡፡

ይቆየን!

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Read more...

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል ዓራት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

       በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

መግቢያ

        የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን ቻይነቱ በሞት ላይ በነበረው ሥልጣንም ገልጿል፡፡ ሞት የኃጢአት ውጤት(ደመወዝ) ነው፡፡ ለሞት ያልተገዛ ፍጥረትም የለም፡፡ ከአዳም ጀምሮ የአዳማዊው ተፈጥሮ ተጋሪ የሆኑ ልጆቹና ለአዳም የተፈጠሩት ፍጥረቶች ሁሉ በሞት ጥላ ሥር ወድቀዋል፡፡ ርዕሳነ አበው፣ነብያት፣ነገሥታት፣ካህናት፣ሁሉ በሞት መዳፍ ተያዙ ማምለጥም የታቻለው ወይም ይህን የሞት ፍርድ ሊያስቀር የቻለ አንድ ስንኳ አልተገኘም፡፡

ይህንኑ ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ ምዕ 5፥12-21 በጥሩ ሁኔታ አብራርቶታል፡፡ "…ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት… ነገር ግነ በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ኃጢአትን ባልሠሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሠ…" ጨምሮም "…የኋላኛው ጠላት የሚሻረው ሞት ነው፤ ሁሉን ከእግሩ በታች አስገዝቶአልና፡፡ነገር ግን ሁሉ ተገዝቶአል ሲል ሁሉን ካስገዛለት በቀር መሆኑ ግልጥ ነው" ፡፡ 1 ቆሮ 15፥25-28 በማለት የሞትን ሥልጣንና የሞትን ሥልጣን ሰብሮ ኃያልነቱን(ሁሉን ቻይነቱን) የገለፀውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥራ ግልፅ አድርጓል፡፡

      አበው ለብዙ ዘመናት ከዚህ የሞት ባርነት ነፃ ሊያወጣቸው ወደሚችል በብዙ ልመና ሲቃትቱ ኖረዋል፡፡ ጊዜው ሲደርስ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ ሞትን ሻረው፡፡ ሞት ነግሦባት በነበረች ምድር ለመጀመርያ ጊዜ " እሰቀላለሁ፣ እሞታለሁ በሦስተኛውም ቀን እነሳለሁ" እንዲሁም " ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል እኔ በፍቃዴ አኖራታለሁ እንጂ ከእኔ ማንም አይወስዳትም፡፡ ላኖራት ሥልጣን አለኝ ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ፤ይህቺን ትዕዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ፡፡" በማለት ሞትን ያስደነገጠ የአዳምን ተስፋ ያረጋገጠ አዋጅ ተሰማ፡፡ ዮሐ 10፥18፣ ማቴ 16፥21

     መግደልና ማዳን የእግዚአብሔር ብቻ ሥልጣን መሆኑ በቅዱሳት መጻሕፍት የተረጋገጠ ነው፡፡ ኦሪ.ዘዳ 32፥39፣ 1ሳሙ 2፥6፣ ማቴ 10፥28-31 ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን "ነፍሴን ላኖራትም ላነሣትም ሥልጣን አለኝ" በማለት በሞት ላይ ያለውን ገዢነቱን በተጨማሪም የመግደልና የማዳን መለኮታዊ ሥልጣን ያለው ወይም እርሱ እራሱ እግዚአብሔር መሆኑን ገለፀ፡፡ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት በዚያች ሰዓትም የተናገረውን አስተውል፡፡ "ኢየሱስም በታላቅ ድምጽ ጮኾ አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ አለ፡፡" ይህ ጩኸት ይህ ቃል የሞትን ሥልጣን ያረጋገጠ የዲያቢሎስ መንግስት የቆረጠ ነው፡፡ ሉቃ 23 ፥46

ልዩ ከምትሆን ቅድስት ትንሣኤው በፊትም በኢየሩሳሌም አውራጃዎች እየተዘዋወረ ሲያስተምር ሙታንን በማስነሳት እርሱ በሞት ላይ ፍፁም ሥልጣን ያለው አምላክ መሆኑን አሳይቶናል፡፡

-    ሉቃ 8፥49-56 ፡- ኢያኢሮስ የተባለው የምኩራብ አለቃ ልጁ በሞተችበት ወቅት ጌታችን በቃሉ አስነስቷታል፡፡ "አንቺ ብላቴና ተነሺ" ብቻ በማለት

 

-    ዮሐ 11፥1-44 ፡- የጌታ ወዳጅ አልዓዛር ሞቶ በተቀበረ በአራተኛው ቀን ጌታችን ትንሣኤና ሕይወት እርሱ መሆኑንና በእርሱ የሚያምን ቢሞትም እንኳ ህያው እንደሚሆን ካወጀ በኋላ ወደመቃብር ሔዶ "አልዓዛር ሆይ ወደ ውጭ ና" በማለት አስነስቶታል፡፡

በዚህ ላይ ምናልባት አንዳንዶች ነቢያት፣ሐዋርያት ድውይ ፈውሰዋል፣ምውት አንስተዋል ይህን አደረጉ ብለን "ሁሉን ቻይ" እንደማንላቸው ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስንም እንዲሁ ነው ብለው ሊከራከሩ ይችላሉ፡፡ 1ኛነገ 17፥17-24፣ 2ኛ ነገ 4፥32-37፣ ሐዋ.ሥራ 9፥40

መልስ

1ኛ- ነቢያትም ሆኑ ሐዋርያት ሙት እስከማንሳት የደረሱት ከልዑል እግዚአብሔር በተሠጣቸው ሥልጣን ጾመው፣ ጸልየው፣ ወድቀው፣ ተነስተው ነው፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ጥቅሶች የሚያመለክቱትም ይህንኑ ነው፡፡ ማር16፥17፣ ሉቃ 10፥17-20፣ዮሐ 14፥12-14፡ እውነት እውነት እላችኋለው በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፣ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል… ማናቸውም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ አደርገዋለሁ፡፡ ያለውን ቃልኪዳን ይጠብቅላቸዋል፡፡ የእርሱ ግን መጾም፣መጸለይ፣ መውደቅ፣መነሣት ሳያስፈልገው በሥልጣኑ ነው፡፡

2ኛ- ከነቢያትም ሆነ ከሐዋርያት ሙት እስከማንሳት የደረሱ ሁሉ በመጨረሻ እነርሱ ራሣቸው በሥጋ ሞት ተይዘዋል፡፡ ጌታችን በትንሣኤ ዘጉባኤ እስኪያስነሳቸውም ይጠብቃሉ፡፡ሙት ያስነሱ እነርሱ ለራሳቸው ግን አስነሺ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እርሱም ትንሣኤ ሕይወት የተባለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ለእርሱ ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ይህንኑም ለማስረዳት ነው ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት ሰዓት እንኳ ብዙ ሙታን ተነስተው በኢየሩሳሌም የታዩት፡፡ በማቴ 27፥51-54 መላእክትም ለሴቶቹ " ሕያዋን ከሙታን መካከል ስለምን ትሹታላችሁ እርሱ በዚህ የለም ተነሥቶአል" ያሉአቸው፡፡ ሉቃ 24፥6

         በእነዚህ ከብዙ በጥቂቱ አእምሮን ለማንቃትና እምነትን ለማፅናት ከተጠቀሱት በተጨማሪ ብዙ የመፅሐፍት ቅዱስ ክፍሎችና የአበው ትምህርት ሁሉን ቻይነቱን አምልተው አስፍተው ገልፀውታል፡፡ ያን በማንበብና በማስተዋል የበለጠ መጠቀም ያስፈልጋል፡፡ በሚቀጥለው አምላካዊ ባህርያት ከሆኑት "ሁሉን አዋቂ" ስለመሆኑ ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም እንማራለን፡፡

ይቆየን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ጥቅምት 2005

Read more...

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ