Login
Main menu

በዓለ ዕረፍቶሙ ለብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ

Index

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን!

ሐምሌ ፭

‹‹ በዓለ ዕረፍቶሙ ለብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ ሐዋርያቲሁ ለክርስቶስ ወአእማዲሃ ለቤተክርስቲያን ››

ሐዋርያ ነጠላ ሲሆን ሐዋርያት ብዙ ቁጥርን ያመለክታል፡፡ ቃሉ ሖረ ከሚለው የግዕዝ ግስ የሚወጣ ሲሆን‹‹ተጓዥ›› ‹‹ሂያጅ›› የሚል ትርጉም ይሠጣል፡፡ የጌታ ሐዋርያት ይህ ስም የተሠጣቸው መልካሙን ዜና ይዘው ወደ ዓለም ሁሉ በመሄዳቸው ነው፡፡‹እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀመዛሙርት አድርጓቸው….››እንዲል ማቴ 28÷19

ሐዋርያት እንደቃሉ ተጉዞው የዓለሙን መልክ ሁሉ ለወጡት፤ ጨለማውን ገፈፉት አልጫውን አጣፈጡት፡፡በምድር በአፀደ ሥጋ ከመኖራቸው ጀምሮ በስሙ ሞትን ተቀብለው ከዚህ ዓለም እስከመለየታቸው ባለው ጉዞ ብርሃንነታቸውን ገልጠው አሳዩ፡፡ጥንታዊት ሐዋርያዊትና ብሔራዊት የሆነችዋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤ/ክ (በሌሎችም ኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያናት ይሔው ትውፊት እንደተጠበቀ ነው) ከራሱ ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከቃሉ የተማሩ የእጁን ተዐምራት ቆመው የተመለከቱ፤በዋለበት እየዋሉ ባደረበት እያደሩ ብዙ ምሥጢራትን የገለጠላቸው፤ በእጆቻቸው የዳሰሱት አብረውትም የበሉና የጠጡ፤ የመከራው የስቅለቱ፣የሞቱ፣የትንሳኤውና የዕርገቱ ቀዳሚ ምስክሮች፤ከራሱ ከባለቤቱም ሥልጣነ ክህነትንና የቤ/ክ አደራ የተቀበሉ በመሆናቸው ‹‹ሐዋርያ›› የሚለው መጠሪያ ከእነርሱ በቀር ለማንም ለማን ቀፅላ አታውቅም፡፡ ከእነርሱ በኋላ የተነሱትን ሁሉ የጠራቻቸውና የምትጠራቸው ሐዋርያነ አበው(Apostolic Fathers) የቤ/ክ ጠበቆች(Apologetics)፣ሊቃውንት፣አበውጳጳሳት፣መምህራን፣ካህናት ወዘተ… በማለት ነው፡፡ እኒህ ሁሉ የሐዋርያትን ሥልጣንና ተግባር ይዘው ቢገኙም ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ለነበሩት የተለየ አክብሮት በመስጠት‹‹ሐዋርያ›› የሚለውን ስያሜ በእነሱ ላይ ብቻ ጠብቃው ኖራለች እንጂ ዛሬ ብዙ ደፋሮች እንደሚጠቀሙበት አይደለም፡፡ በነቢያትም እንዲሁ ነው፡፡

ስለ ሁሉ ሐዋርያት የሕይወት ገድል ለመተረክ ጊዜም አይበቃም አቅሜም አይፈቅድም፡፡ ነገር ግን ሐዋርያት ሁሉ ስለተወከሉባቸው ሁለቱ ታላላቅ ሐዋርያት ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ በመጠኑ ማለት እወዳለሁ፡፡አንዱ የሕዝብ ሌላኛው የአሕዛብ ሐዋርያ ናቸውና፡፡ ከዚህ የወጣ የለም፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ ከዓሣ አጥማጅነት ቅዱስ ጳውሎስ ከደማስቆ መንገድ እንዴት እንደተመረጡ፤የቅዱስ ጴጥሮስን የተለምዶ ሕይወትና ቅዱስ ጳውሎስ ምሁረ ኦሪትነት ለመተረክም አልሻም፡፡ ብዙዎቻችን የምናውቀው ነውና፡፡ ሁለቱም የተሠጣቸውን አደራ በትጋት ፈጽመው ናፍቆታቸው ተፈፅሞላቸዋል፡፡

ማንሳት የምፈልገው ከእነርሱ ሕይወት እኛ የምንማረው ምንድር ነው?የሚለውን ነው፡፡

 ሊቀ ሐዋርያትበዕድሜውም አዛውንት እንደመሆኑ ከጌታም ጋር ብዙ ጊዜ እንደማሳለፉም ቅድሚያ የቅዱስ ጴጥሮስን ሕይወት በጨረፍታ እንዳስሳለን፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹በዓሣ ፋንታ ሰውን የምታጠምድ አደርግሃለው›› ተብሎ ከተጠራበት ሰዓት አንስቶ ከጌታችን ጋር ማስመሰል በሌለበት ሕይወት ኖሯል፡፡ ከጌታችን የተሠወረ ምንም ነገር እንደሌለ የታወቀ ነገር ቢሆንም ቅሉ፤ ቅዱስ ጴጥሮስ ግን ከራሱ በሚወጣ የዋህነትና ቅንነት በጎም ሆነ የሚነቀፍ ጠባዩ በጌታ ፊት የተገለጠ ነበር፡፡ በወንጌል የተፃፈው የቅዱስ ጴጥሮስ ሕይወት፤ ጥንካሬው ብቻ ሳይሆን ድክመቱ፣ስህተቱም ሆነ እውቀቱ፣ማስተዋሉም ሆነ ችኩልነቱ ብዙ ትምሀርት ትቶልን አልፏል፡፡ከጌታችን ጋር የነበረ ሕይወቱ በመውደቅና በመነሳት  የተሞረደየተቃናና የዳበረ ሐዋርያ ነው፡፡

ታላቁ ውድቀቱ ለታላቁ ትንሣኤው ምክንያት መሆኑን ማስተዋል ምን ያህል ያፅናናል፡፡ ምን ያህል ተስፋ መቁረጥን  ይሠብራል፡፡የቅዱስ ጴጥሮስ አዲስ ሕይወት ጅማሬ በጥብርያደስ ባህር ከጌታ ጋር ከነበረው ቆይታ ይነሳል፡፡ ‹‹የዮና ልጅ ስምኦን ትወደኛለህን?›› የምትለዋ ጥያቄ ለቅዱስ ጴጥሮስ ሕይወት ወሳኝ ነበረች፡፡ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ጴጥሮስን ለታላቅ አገልግሎት ኃላፊነት ሊሠጠው ፈቃዱ ሆኗል፡፡ግን በእርሱ እርግጠኛ መሆን ይፈልጋል፡፡ እርሱም በሰጠው ምላሽ ፈተናውን አልፏል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታን ሦስት ጊዜ መካድና መፀፀት፤ የመድኃኒታችንም የይቅር ባይነቱ ስፋት ቅዱስ ጴጥሮስን ደግሞ ለተሻለ ሕይወት ወለደው፡፡ከውድቀቱ የተነሳ የተሻለ ጠንክሮ የተሻለ አስተውሎ የተሻለ ተቀርጾ ነበር የተነሳው፡፡ ዮሐ 21

የቅዱስ ጴጥሮስ ሕይወት በዚያች ቃል ታሠረች፡፡ ‹‹አንተ ሁሉን ታውቃለህ እንድወድህም አንተ ታውቃለህ›› በምትለዋ ቃል፡፡ ከዚያ ለጥቆ በነበረ ሕይወቱ መልሱ ይኸው ነበር፡፡ ስለምን ትሰብካለህ?ስለምን ትፀልያለህ?ስለምን ታመሠግናለህ? ስለምን ትታሠራለህ?ስለምን ትገረፋለህ?ስለምን ትሞታለህ? ስለምንስ ትኖራለህ?ወዘተ… ብለን ብንጠይቀው መልሱ ምክንያቱም ‹‹ስለምወደው››  የሚል ነው፡፡ በአንተስ ላይ ስለምን ይህ ሁሉ ይደርስብሃል ብንለው ‹‹ለእርሱ ባለኝ ፍቅር ላይ እርግጠኛ ስለሆነ›› የሚል መልስ ይሰጠናል፡፡

ጌታችን ሐዋርያቱን በቃሉ ላይ የሾማቸውና ትምህርታቸውን በብዙ ድንቅ ተዓምራት ያፀና የነበረ እንዲሁ አይደለም፡፡ወደ እስራት፣ወደ ግርፋት፣ ወደ መከራ፣ ወደ ሞት፣ የወሰዳቸውም ለእርሱ ባላቸው ፍቅር እርግጠኛ ስለሆነ ነው፡፡ እኛስ ጋር ያለው እንዴት ነው?

ጸሎታችን፣ምስጋናችን፣ጾማችን፣ምጽዋታችን … ወዘተ አጠቃላይ ክርስቲያናዊ ሕይወት የምንኖረው ለምንድነው? አገልጋዮችስ የምንቀድሰው፣ ሕፃናትን የምናጠምቀው፣ በሰዓታት በማኅሌት የምናድረው፣ የምንሰብከው ወዘተ… ለምንድር ነው? በዚህ ሁሉ እኛ ለክርስቶስ ያለንን ፍቅር እገልጣለን ወይስ የልማድ እስረኞች ነን፡፡


Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ