ትውልዱ ከእመቤታችን ምን ይማራል?
Index
2ኛ.ሃይማኖት፡- ከወላዲተ አምላክ ማርያም አንዱ የተማርነው ሃይማኖት ነው፡፡ከእርሷ በፊት ያልሆነ ከተፈጥሮ ሥርዓት የተለየ ያለወንድ ዘር መጽነስ እና በድንግልና መውለድ በመልአኩ ሲነገራትና ይህ ይሆን ዘንድ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም ሲላት ፈቃዷን በሃይማኖት ገልጣለች፡፡ ፍጹም እምነት ማለትም ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም ብሎ ማመን ነው፡፡
በቃና ዘገሊላ ሠርግ ለልጇ የወይን ጠጅ ማለቁን ከነገረችው በኋላ ላገልጋዮች በፍጹም እምነት የሚላችሁን አድርጉ ብላቸዋለች፡፡ በዚያ ደቂቃ ለዚያ ሁሉ ሠርገኛ የሚሆን ወይን ከየት ያመጣል? ምን መፍትሄ ሊኖር ይችላል?የመሳሰሉት የጥርጥር ሀሳቦች በእርሷ ዘንድ አልነበሩም፡፡ ሁሉን ቻይ መሆኑን ከቀድሞም አውቃና አምና ትኖር ነበርና፡፡
ዛሬ ያለውንየዓለም አካሄድ በእምነት ካልሆነ ማሸነፍ አይቻልም፡፡ከተስፋ መቁረጥ የተነሳ ጨለማው የማያልፍ ደመናው የማይገፍ የሚመስላቸው ብዙዎች ይኖራሉ፡፡ እምነት ማለት በእግዚአብሔር ኃይል የማይቻለው ይቻላል ይሆን የማይመስለው ይሆናል ብሎ ማመን ነው፡፡ የተፈጥሮ ህግ፣ አመክንዮ ወዘተ… እዚህ ቦታ የላቸውም፡፡ የእርሱ ሥራ ከዚህ ሁሉ በላይ ነውና፡፡
3ኛ. ፍጹም ታዛዥነት፡- እመቤታችን ፈቃዷ ሁሉ ለልጇ የተሰጠ ነበር፡፡ ከእርሱ የተለየ ሀሳብ ወይም ፈቃድ አልነበራትም፡፡ ራሷን ፈጽማ ለእግዚአብሔር ያስገዛች ብላቴና ስለነበረች የመልአኩን ብሥራት የተቀበለችው የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲፈጸም ራሷን በመስጠት ነው፡፡ ከቀደምት ነቢያት እግዚአብሔር ፈቃዱን ለመፈጸም ሲልካቸው ሲጠራቸው ምክንያት በማንሳት ወደኋላ ለማለት የሞከሩ ነበሩ፡፡ እግዚአብሔር ለሚጠራን አገልግሎት መሠማራት ክብር እንደሆነ ሁሉ ታላቅ ሸክምና ኃላፊነትም ነው፡፡ እመቤታችን ለእናትነት ስትመረጥ ታላቅ ክብር መሆኑ ቢታወቅም ‹‹በነፍስሽ ሰይፍ ያልፋል›› እስኪባል የደረሰ ታላቅ ኃላፊነትም ነበር፡፡ በፍጹም ታዛዥነትም እስከ ፍጻሜ ኃላፊነቷን ተወጥታለች፡፡ በመጨረሻም በመስቀል ላይ ሳለ በፈቃዱ ወደ እርሱ እስኪወስዳት ድረስ በዮሐንስ ዘንድ እንድትኖር ሲነግራት በጊዜው ወድቆባት የነበረ ነፍስን የሚወጋ ሀዘን ለቃሉ ያላትን ታዛዥነት አልለወጠውም፡፡
4ኛ.ጥበብ መንፈሳዊ፡- እመ አምላክ ብሥራተ መልአክን በተቀበለችበት ወቅት ቅዱስ ገብርኤልን ትጠይቀው የነበሩ ጥያቄዎች ፍጹም ጥበብ መንፈሳዊ የተሞሉነበሩ፡፡ ከጉባዔ ያልዋሉ ምሥጢር ያላደላደሉ የመጽሐፍ ቅዱስ የከንፈር ወዳጆች የእመቤታችንን ጥያቄዎች የጥርጥር ያለማመን አድርገው ሲያቀርቡ እነሆ እንሰማቸዋለን፤እኒህ የወንጌሉ ምሥጢር የተከደነባቸው ናቸው፡፡እመቤታችን የጠየቀቻቸው ጥያቄዎች የተገቡና ነገረ ሥጋዌን የበለጠ እንዲብራራ ያደረጉ ናቸው፡፡ እመቤታችን ጥያቄዎቹን ባትጠይቅ ኖሮ፡-
ሀ. ከእርሷ የሚወለደው ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑ
ለ. በድንግልናና ያለወንድ ዘር የተጸነሰና የሚወለድ መሆኑ
ሐ. ለአበው በተሰጠው ተስፋና በትንቢተ ነቢያት መሠረት የዳዊት ዘር መሆኑና የያዕቆብን ወገን ለዘላለም የሚገዛ መሆኑ፡
መ. ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ መወለዱ በግብረ መንፈስ ቅዱስ መሆኑ
ሠ. አብ ሊያፀናት ወልድ ለተዋሕዶ(ሥጋን ለመንሳት)መንፈስ ቅዱስ ሊከፍል ሊያዋሕድ እንደሚያድሩባት ተለይቶ ባልታወቀ ነበር
ረ. የሚወለደው ሕጻን ስሙ ኢየሱስ እንደሚባልና ሕዝቡን ሁሉ ከኃጢአት ከመርገም ከፍዳ የሚያድናቸው መሆኑ
ሰ. ራሷ እመቤታችን በንጽሕናና በቅድስናዋ ከሴቶች ሁሉ ተለይታ የከበረች መሆኗ
ሸ. ነቢየ ልዑል ዐርኩ ለመርዓዊ የተባለ የዮሐንስ መጥምቅ በእግዚአብሔር ድንቅ ተዐምራት ከዘካርያስና ከኤልሣቤጥ መፀነስ፤ኤልሳቤጥ በብፅዐት ብትሰውረውም የተገለጠ በእመቤታችን ጥያቄ ነው፡፡
ብዙ ጠይቀን ጥቂት መልስ ለማናገኝ ለእኛ የጥያቄ አቀራረብን አቅል(ሥርዓት) እንረዳበት ዘንድ ታላቅ ትምህርት ነው፡፡በአግባቡ ያልቀረበ ጥያቄ መልስ አይኖረውምና፡፡
5ኛ. መናፍስትን መመርመር፡-‹‹መንፈስን ሁሉ አትመኑ፤ነገር ግን መናፍስት ከእግዚአብሔር ሆነው እንደሆነ መርምሩ››እንዲል፤እመቤታችን መልአኩ ተገልጦ የምስጋና ሰላምታ ባቀረበላት ጊዜ ወዲያውኑ አልተቀበለችውም፡፡መተርጉማን‹‹እናቴሔዋንን ያሳተ ሰይጣን…››ብላ አሰበች እንዲሉ ዛሬ ትንቢት ተናጋሪ፣ ራዕይ ተመልካችና ሕልም ሀላሚ በበዛበት ጊዜ፤ ብዙዎቻችንም በመናፍስት አሠራር የሚሆነውን ሳንመረምር በምናያቸው ድንቃ ድንቆች የሰዎችን እውነተኛነትና ቅድስና በምንመዝንበት ሰዓት ከተወዳጇ እናታችን እንዲህ ያለውን የመጠበቅ ጥንቃቄ ልንማር ያስፈልጋል፡፡1ዮሐ4፥1
6.ጭምትነት፡-እመቤታችን እንዴት ባለ ጭምትነት በንጽሕና በቅድስና እንዳደገች አባ ሕርያቆስ ሲናገር ‹‹ ኦ ድንግል አኮ በተላህዮ ዘልሕቂ ከመ አዋልደ ዕብራውያን እለ ያገዝፋ ክሣዶን አላ በቅድስና ወበንጽሕ ውስተ ቤተ መቅደስ ነበርኪ›› ድንግል ሆይ አንገታቸውን እንደሚያገዝፉ እንደ ዕብራውያን ሴቶች ልጆች በዋዛ ያደግሽ አይደለም በንጽሕና በቅድስና በቤተ መቅደስ ኖርሽ እንጂ በማለት ገልጿል፡፡ ከቅዱስ ገብርኤል ከኤልሳቤጥና ከጻድቁ ዮሴፍ ጋር በነበራት ጊዜ፤ ስምኦን አረጋዊ ጌታን ባቀፈውና ትንቢት በተናገረበት፤ በአሥራ ሁለት ዓመቱም በቤተ መቅደስ በጠፋባቸው ወቅት፤ እንዲሁም በጊዜ ስቅለቱ በደረሰባት ሀዘን ወዘተ…ጭምትነቷ በሚያስደንቅ ሁኔታ ታይቷል፡፡በእያንዳንዱ ሁኔታ የምታደርገው እንቅስቃሴም ሆነ ንግግር ፍጹም ጸጋን የተላበሰ ነበር፡፡ጥያቄዋ፣ ሰላምታዋ፣ ቅሬታዋንም ሆነ ሀዘኗን ትገልፅበት የነበረበት መንገድ በፍጹም ጭምትነት የተጌጠ ነበር፡፡ በመልአኩ እንደተነገራት በኤልሳቤጥም እንደተመሰከረላት የእስራኤል ተስፋ ከእርሷ እንደሚወለድ የታወቀ ቢሆንም ቸኩላ ይህን ምስጢር ለማንም አልገለጠችም፡፡ እርሱ በሚፈቅደው መንገድ ራሱን እስኪገልጥ በጭምትነት ጠበቀች እንጂ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በክርስቶስ ላመኑ ክርስቲያን ሴቶች ሊመክር የሚገባውን ሲነግረው ‹‹…ሴቶች ጭምቶች፣የማያሙ፣ልከኞች፣በነገር ሁሉ የታመኑ ሊሆኑ ይገባቸዋል›› ብሎታል፡፡ 1ኛ ጢሞ3÷11 ቅምጥሊቱ ሴት ግን በሕይወቷ ሳለች የሞተች ናትና፡፡1ኛ ጢሞ5፥8 የክርስቲያን ሴቶች በሥራቸውም ሆነ በአነጋገራቸው በአለባበሳቸውም ሆነ በአካሄዳቸው ራሳቸውን በጭምትነት እንዲገልጹ ከእመቤታችን በላይ አርአያ ሊሆን የሚችል አይሰጣቸውም፡፡