ትውልዱ ከእመቤታችን ምን ይማራል?
Index
7. ማኅበራዊ ሕይወት፡- እመብርሃን ቅድስት ድንግል ማርያም የኤልሳቤጥንመጽነስ ከመልአኩ እንደሰማች ፈጥና ነው ወደ ኤልሳቤጥ የሄደችው፡፡ ያቺ እግዚአብሔርን በመፍራት የምትኖር የካህን ሚስት ስእለቷ ተሰምቶ በመልአክብሥራት ወንድ ልጅ መጽነሷን ስትሰማ ደስታዋን ለመካፈል አልዘገየችም፡፡ በሰው ሀዘን ተደስቶ በባልንጀራው ደስታ የሚከፋ በበዛበት በዚህ ክፉ ዓለም የእርሷን አርአያ መከተል ምንኛ መቀደስ ነው፡፡ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ደስ ከሚላቸው ጋር ደስ ይበላችሁ፣ከሚያዝኑም ጋር አልቅሱ››ያለው የሰውን ስሜት በቅንነት መካፈልክርስቲያናዊ ምግባር በመሆኑ ነው፡፡ሮሜ 12፥15፤ ሉቃ 1፥57-65
ከእግዚአብሔር የሆነን ነገር ደግሞ የሰዎቹን ደስታ ከመካፈል ባለፈ ማድነቅ ይገባል፡፡ለኤልሳቤጥ ከእግዚአብሔር እንደሆነው ሁሉ ለሕዝቡ ጥቅም ከእግዚአብሔር የሆነ ስጦታ(ጸጋ) የተሰጣቸው ስንመለከት
ሀ. እግዚአብሔር በእነርሱ አድሮ ስለሠራው ድንቅ ሥራ
ለ.እግዚአብሔር በእርነሱ አድሮ ሕዝቡን ስለመጥቀሙ
ሐ.በዘመናችንም ዓይኖቻችን የእርሱን ድንቅ ሥራ በማየታቸው ልንደሰት ይገባናል፡፡ ከእግዚአብሔር በሆነ ጸጋ መቅናት፤ሰዎቹ ለሚሠሩትም ሥራ እንቅፋት መሆን ከእግዚአብሔር ጠላቶች ጋር መሰለፍ ነው፡፡
8. ድንግልና፡- የእመቤታችን ድንግልና፡-
ሀ. በሥጋ በኅሊና በመሆኑ( ድንግል በኅሊናኪ ወድንግል በሥጋኪ) እንዲል
ለ.ሕዋሳቶቿ በሙሉ የተጠበቁ መሆናቸው ማለት የኃጢአት መግቢያ ከሆኑት ከርዕይ ከሰሚዕ ከገሢሥ ከአጼንዎ የተጠበቀች መሆኗ( ከማየት፣ከመስማት፣ከመዳሰስ፣ከማሽተት)
ሐ.ቅድመ ጸኒስ ጊዜ ጸኒስ ድኅረ ጸኒስ ፤ቅድመ ወሊድ ጊዜ ወሊድ ድኅረ ወሊድ ድንግልናዋ ለቅጽበት ያልተለወጠ መሆኑ(ድንግልናዋ እናት በመሆኗ ያልተለወጠ መሆኑ)ልዩ ያደርጋታል፡፡ይህ ለሌሎች ሴቶች አይቻልምና‹‹ከሴቶች ተለይተሸ››ያሰኛት ቅሉ አንዱ ይህ ነው፡፡
በተፈጥሮ ሥርዓት አንዲት ሴት ሙሽራዋን እስክታገኝ(እስኪመጣ)ራሷን በመግዛት እንደምትጠብቅ፤ ያ ካልሆነ ግን ከክብር እንደምታንስ በመንፈሳዊው ሕይወትም ነፍሳችንን በኃጢአት ከክብር ከማነስ ጠብቀን ድንግልና የተባለ ልጅነታችንን በሃይማኖት በምግባርሙሽራችን የሆነው ክርስቶስ እስኪመጣ እንጠብቃለን፡፡
ለእርሱ ለክርስቶስ የሸለመች ሙሽራ ሆነን እንዴት ባለ የነፍስ ቅድስና መጠበቅ እንዳለብን የተሰጠችን ሕያው ምሳሌ ደግሞ እመቤታችን ነች፡፡ በእርሷ በአካል ያደረ በእኛ በጸጋ ያድርብናልና፡፡የዮሐ.ራዕ 21፥2
9.ጸሎት፡- እመቤታችን የመልአኩን ብሥራት የኤልሳቤጥንና የዮሐንስን ምሥክርነት ከተቀበለች በኋላ የተናገረችው ጸሎት በዘመናት በአላውያን ነገሥታት በአረማውያን እንዲሁም በመናፍቃን የተነሣባትን የጥፋት ማዕበል ለመሻገር ለቤተክርስቲያን ጉልበት የሆነ ነው፡፡ጸሎቷም ምን ያህል በቅዱሳት መጽሐፍት እውቀት የበለጸገ የልዑሉንም ሥራ በማስተዋል የከበረ መሆኑ ተገልጦ የሚታይ ነው፡፡ ፍጹም በነፍሷ ለእግዚአብሔር ያላትን ክብር፣ ትኁታኑን የማይረሳ መሆኑን፤ ቅድስናውን፣ እውነተኛ ፈራጅ መሆኑን፣ለሚፈሩት የሰጣቸውን ቃል ኪዳን የማይረሳና ምህረቱም ለልጅ ልጅ መሆኑን የገለጠ ነው፡፡በከንፈር እግዚአብሔርን የሚያከብሩና በነፍሳቸው ልዑሉን የሚፈሩ የጸሎታቸው ልዩነት ለማነጻጸር ከሚቻል በላይ ነው፡፡ ጸሎተ ማርያም ዛሬም ድረስ በቤተክርስቲያን ለካህናት ሞገስ ለሕሙማን ፈውስ፤ ለሀገር ሰላም ለርኁባን ምግብ፤ለመምህራን ጽናት ለደቀመዛሙርት እውቀት የሆናቸው ለዚህ ነው፡፡ሐዋርያትም በጸሎታቸው ወቅት እርሷን ይዘው መጸለያቸው የጸሎታቸው ምላሽ ይፈጥን ዘንድ ነው፡፡የእርሷ ጸሎት ተሰሚ ጉዳይ ፈጻሚ መሆኑን በቃና ሠርግ በግልፅ ማየት ይቻላል፡፡ ‹‹የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም››ብላ ለልጇ ከነገረችው በኋላ ድጋሚ መጠየቅ አላስፈለጋትም ‹‹የሚላችሁን አድርጉ›› አለች እንጂ፡፡ ደራሲ‹‹አልቦ ጸሎት ወአልቦ ትንባሌ እንበሌኪ ድንግል ዘየዐርግ ሉዐሌ››ያለ ይህን ማስተዋል በመቻሉ ነው፡፡በመሆኑም እመቤታችንን ሳትይዝ ጸሎት ልመና አቀርባለሁ የምትል ቤተክስቲያን ብትኖር እርሷ ሐዋርያት የሰበሰቧት ቤተክርስቲያን አለመሆኗ በዚህ ይታወቃል፡፡
0. ምስጋና፡- እመቤታችን በእርሷ ላይ ይሆን ዘንድ ልዑሉ የፈቀደው ከሆነ በኋላ ይህን የተረዱ እነ ኤልሳቤጥ በተፀውዖ ስሟ ማርያም ብለው መጥራታቸውን እንደማይገባ ድፍረት አድርገውስለቆጠሩት፤ የእርሷም ከቤታቸው ጣሪያ በታች መግባት የተገባቸው እንዳልሆነ ስለተረዱት‹‹የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል?››በማለት ክብሯን ገልጠው መሰከሩ፡፡እመቤታችን ጌታን ፀንሳ ከወለደች በኋላ በወንጌል እንዲሁ ‹‹ማርያም›› ተብላ ስትጠራ አናገኝም፡፡ወንጌላውያኑ ሁሉ ‹‹የሕጻኑ እናት›› ‹‹የኢየሱስ እናት›› ‹‹ሴቲቱ››እያሉ ሲጠርዋት ነው የምናየው፡፡ ሁሉም መጠሪያዎች የነቢያትን ትንቢት መፈጸም የሚያሳዩና የሥጋዌን ምሥጢር ያዘሉ ናቸውና፡፡ይህን የተረዱ ሊቃውንት‹‹እመ አምላክ፣ ወላዲተ አምላክ፣እመ ብርሃን ወዘተ…››እያሉ መጥራቻቸው ወንጌላውያንን አብነት አድርገውነገረ ሥጋዌን ለመግለጽና ክብሯን ለመመስከር ነው፡፡
እመቤታችን በኤልሳቤጥ ቤት የሆነውን ካየች በኋላ‹‹ለእኔ(በእኔ)ታላቅ ሥራን አድርጓልና ስሙም ቅዱስ ነው›› ስትል አመስግናለች፡፡ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስብሎ ማመስገን በዓለመ መላእክት የተለመደ ነው፡፡የመላእክት እህት የሆነች እመቤታችንም ከነፍሷ የሆነ ምስጋናዋን በዚሁ ሰማያዊ በሆነ ምስጋና ገልጻለች፡፡ ይህም ከመላእክት ጋር የነበራትን የምስጋና ኅብረት ያሳያል፡፡ከዚህም በግላችንም ሆነ ለፍጥረተ ዓለም ለተደረገው የእግዚአብሔር የቸርነቱ ሥራ ማመስገን የተገባ መሆኑን ለሁላችን ትምህርት ትታልናለች፡፡
እመቤታችን ፈጣሪዋናአምላኳ እንዲሁም ልጇ የሆነውን እርሱን ማመስገን ብቻ ሳይሆን፤በእርሷ ላይ በተደረገው ድንቅ ነገር ትውልድ ሁሉ ሲያመሰግኗት ሲያደንቋት እንደሚኖሩም ገልጻለች፡፡በዚህም የተነሳ እውነተኛዋ የሐዋርያት ቤተክርስቲያን ልዑል እግዚአብሔርን ከማመስገን ለጥቃ እመቤታችንን በውዳሴ በቅዳሴ በማንሳት ታመሰግናለች፡፡ ልጆቿም በነገር ሁሉ በንጽሕናና በቅድስና በማጌጥ እናታቸውን ቅድስት ድንግል ማርያምን እንዲመስሉ ታስተምራለች፡፡ ቤተክርስቲያን በማኅሌቱ በቅዳሴው በሰዐታቱ በስብከቱና በትምህርቱ ሁሉ ደጋግማ እመቤታችንን የማንሳቷ ምስጢር በንጽሕናና በቅድስናዋ አብነት በመሆን በአማላጅነቷም ፍጹምነት ወደ እግዚአብሄር እቅፍ የምታደርሰን በመሆኗ ነው፡፡
ከጥንት ሲወርድ ሲወራረድ የመጣው ትክክለኛ ዶግማ ቀኖናና ትውፊት እንዳይበረዝ እንዳይከለስ በማስተማር ጠብቃ ማቆየቷ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያንን ከማንም በላይ ሐዋርያት ከጌታችን የተቀበሉት የጥንታዊውና የእውነተኛው ክርስትና የታመነችባለ አደራ ቤተ መዘክር ያደርጋታል፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር!
እንኳን ለጾመ ፍልሰታ ለማርያም በሰላም አደረሰን!
ቀሲስ ታምራት ውቤ
ነሐሴ 2007 ዓ.ም